Wednesday, July 29, 2015

የዞን 9 ጦማርያን በድጋሚ ለብይን ተቀጠሩ

በእነ ሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ተመስርቶባቸው ጉዳያቸው ከአንድ አመት በላይ እየተጓተተ ከሚገኙት አራቱ የዞን 9 ጦማርያን ለነሀሴ 13/2007 ዓ.ም ለብይን ተቀጥረዋል፡፡
ዛሬ ሐምሌ 22 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ "ፍርድ ቤት" ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ጦማርያኑ በተከታታይ ቀጠሮ በተሰጠበትና እልባት ባላገኘው ‹ተከሳሾች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ይሰናበቱ ወይስ ይከላከሉ› በሚለው ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ፍርድ ቤቱ ሌላ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው የአቃቤ ህግ የደረጃ ምስክሮች ቃል ከመቅረጸ ድምጽ ተገልብጦ በጽሁፍ ከመዝገቡ ጋር መያያዙን ለመጠባበቅ ነበር፡፡ በዚህም ፍርድ ቤቱ የምስክሮቹ ቃል በጽሁፍ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር መያያዙን በመግለጽ መዝገቡን መርምሮ ተከሳሾች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ይሰናበቱ ወይስ መከላከል ያስፈልጋቸዋል የሚለውን ለመበየን ለነሀሴ 13/2007 ቀጠሮ ይዟል፡፡
የተሰጠው የቀጠሮ ጊዜ ረዘመ በሚል ቀጠሮው አጭር እንዲሆን የተከሳሾች ጠበቃ ቢጠይቁም ፍርድ ቤቱ ‹‹ከተያያዘው የመዝገብ ብዛት አንጻር ከነሀሴ 13/2007 በፊት አይደርስልንም›› በማለት የተሰጠው ጊዜ ምክንያታዊ እንደሆነ ለማስረዳት ሞክሯል፡፡ ጠበቃው በበኩላቸው ‹‹መዝገቡ ብዙ ቢመስልም የተጠቀሰውን ያህል ጊዜ ሊወስድ አይችልም ብለን ስለምናምን አጭር ቀጠሮ ይሰጠን፤ በሌላ በኩል ክሱ ከተቋረጠላቸው ሰዎች ጋር በተያያዘ መዝገቡ እንደቀነሰ እናምናለን›› በማለት መዝገቡ ከተባለው ጊዜ በፊት ተመርምሮ ብይን ሊሰጥ ይገባል በሚል አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በእስር የሚገኙት ጸሃፊዎች አቤል ዋበላ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና በፍቃዱ ዘ ኃይሉ
ሆኖም ግን ፍርድ ቤቱ ከነሀሴ 15/2007 ዓ.ም በኋላ እንደማይሰየም በመግለጽ፣ ከዚያ በፊት ነሀሴ 13/2007 ዓ.ም ብይኑን ለማድረስ፣ ካልተቻለ ደግሞ እስከ 15/2007 ባሉት ሁለት ቀናት ለመጨረስ እንደሚሞክር በመግለጽ ቀጠሮውን በነሀሴ 13/2007 ዓ.ም አጽንቷል፡፡
በዛሬው ውሎ ከቂሊንጦ እስር ቤት በፍቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ አቤል ዋበላና ናትናኤል ፈለቀ የቀረቡ ሲሆን አሁን በክስ ላይ ከሚገኙት ውስጥ አንደኛ ተከሳሽ የሆነችው ሶልያና ሽመልስ በሌለችበት ጉዳያቸው ለአጭር ጊዜ ታይቷል፡፡
የዞን9 ማስታወሻ
የዞን9 ጦማርያንን የፍርድ ቤት ሂደት በማገተት ያልተሰራ ወንጀልን መፍጠር አይቻልም፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ጉዳን ማንጋተቱን ያቆም ዘንድ የመንግስት ስራ አስፈጻሚ አካላት በጉዳዬ ላይ ውሳኔያቸውን በአፋጣኝ እንዲሰጡልን ለመጠየቅ እንወዳለን፡፡
#Ethiopia #FreeZone9Bloggers 

Monday, July 20, 2015

‹‹ፍርድ ቤቱ›› የዞን 9 ጦማርያንን ጉዳይ ማጓተቱን ቀጥሏል

 #Ethiopia #FreeZone9Bloggers
አንድ አመት ከሦስት ወር በእስር ላይ ያሉትና በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ ቀርቦባቸው ጉዳያቸው እየታየ የሚገኙት የዞን 9 ጦማርያን ለ31ኛ ጊዜ ዛሬ ሐምሌ 13/2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ቀርበው ለ32ኛ ጊዜ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

መዝገቡ ለዛሬ ተቀጥሮ የነበረው ተከሳሾች የቀረበባቸውን ክስ ይከላከሉ ወይስ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ይሰናበቱ የሚለውን ለመወሰን ነበር፡፡ ሆኖም ግን ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ የደረጃ ምስክሮች ቃል በጽሑፍ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር አልተያያዘልኝም በሚል መዝገቡን መርምሮ ብይን ለመስጠት እንዳልቻለ በመግለጽ አራቱ ጦማርያን ላይ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ እንደገለጸው እስካሁን በ30/07/07 ዓ.ም በዋለው ችሎት ወቅት የተሰሙት የአቃቤ ህግ የደረጃ ምስክሮች ቃል በጽሁፍ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር አልተያያዘም፡፡ በተጨማሪም ሰኔ 8/2007 ዓ.ም በአንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ ላይ በቀረበው የአቃቤ ህግ ማስረጃ (ሲ.ዲ) ላይ ፍርድ ቤቱ በሰጠው ብይን ላይ የተከሳሽ ጠበቆች ያቀረቡት አቤቱታም እንዲሁ በጽሁፍ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር እንዳልተያያዘ ተገልጾዋል፡፡

በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ዛሬ ይሰጠዋል ተብሎ ይጠበቅ የነበረውን ብይን በማራዘም የጦማርያኑን ጉዳይ ማጓተቱን ቀጥሏል፡፡ በዚህ መሰረትም ሐምሌ 22/2007 ዓ.ም የተጠቀሱት የምስክሮች ቃል እና የጠበቆች አቤቱታ በጽሁፍ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር መያያዙን ‹‹ለመጠባበቅ›› ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በዚህም በተከሳሾች ላይ የሚሰጠው ብይን ማራዘሙ ተመልክቷል፡፡ ይህን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ተከትሎ 5ኛ ተከሳሽ አጥናፍ ብርሃኔ፣ ‹‹450 ቀናት በእስር ቆይተናል፤ እኛም ቤተሰቦቻችንም እየተጉላላን ነው፡፡ ይህን ከግምት በማስገባት ብይን ለመስማት አጭር ቀጠሮ ይሰጠን›› ሲል ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ለብይን ሳይሆን ‹ከመዝገቡ ጋር መያያዙን ለመጠባበቅ› ‹‹አጭር›› ያለውን ቀጠሮ ለሐምሌ 22/2007 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡

በሌላ በኩል ሐምሌ 1/2007 ዓ.ም ድንገት የፍርድ ቤት ቀጠሯቸው ሳይደርስ ‹‹ክሳችሁ ተቋርጧል›› በሚል ከእስር የተለቀቁት ጦማርያንና ጋዜጠኞች ዛሬ በቀጠሯቸው መሰረት ችሎት ፊት ቀርበዋል፡፡ ተፈችዎቹ ፍርድ ቤቱ በይፋ እንዳላሰናበታቸው በማሰብ ‹‹በእነ ሶልያና ሽመልስ!›› የሚለው የዳኞቹ ጥሪ ሲሰማ በእስር ላይ ከሚገኙት ጓደኞቻቸው ጋር ከመቀመጫቸው በመነሳት ችሎት ፊት የቀረቡ ሲሆን፣ ዳኞቹ በመካከልም ‹‹የሌሎቻችሁ ክስ ተቋርጧል›› በማለት አልፈዋቸዋል፡፡

ሆኖም ግን አምስቱ ተፈችዎች ለእስር በተዳረጉበት ወቅት ቤታቸው ሲፈተሽ በኤግዚቢትነት እና በሰነድ ማስረጃነት በፖሊስ የተያዙባቸው እቃዎቻቸው እንዲመለሱላቸው ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ ማቅረባቸው ተገልጾዋል፡፡ ተፈችዎቹ አቤቱታቸውን ቀደም ብለው በጽ/ቤት በኩል አስገብተዋል፣ ፍርድ ቤቱም አቤቱታቸው እንደደረሰው በመግለጽ ትዕዛዝ እንደሚሰጥበት አስረድቷል፡፡

በዛሬው የችሎት ውሎ ከቂሊንጦ እስር ቤት የቀረቡት በፍቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔ፣ ናትናኤል ፈለቀ እና አቤል ዋበላ ያለውን ኢ-ፍትሃዊነት ለመቃወም ጥቁር ቲሸርት ለብሰው ፍርድ ቤት ለመቅረብ ሞክረው የነበር ቢሆንም በእስር ቤቱ አስተዳደር መከልከላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የዛሬውን የፍርድ ቤት ውሎ በርካታ የጦማርያን ወዳጆች፣ ቤተሰቦቻቸው፣ ጋዜጠኞችና ዲፕሎማቶች ተከታትለውታል፡፡ በቅርቡ የእስር ጊዜዋን አጠናቅቃ ከእስር የተፈታችው ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙም ችሎቱን ታድማለች፡፡

የዞን9 ማስታወሻ 
አራቱ በእስር ላይ የሚገኙት ጦማርያንን እና ቤተሰባቸውን በማጉላላት እና ፍትህ በመንፈግ የሚሰበር ሞራል የላቸውም ፡፡ ሆነ
ተብሎ በሚደረገው በዚህ የፓለቲካ ውሳኔን የመጠበቅ ሂደት የሚባክነው የወጣቶች እድሜ አሁንም ባይሆን አንድ ቀን የህሊና ዋጋ እንደሚያስከፍል ለዳኞች ለማስታወስ እንወዳለን፡፡ ቀላሉ እርምጃ ቀሪውን የሌለውን ማስረጃ በመመርመር ሰበብ ከማጉላላት ይልቅ አራቱን ጦማርያን መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነጻ ማሰናበት ነው ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ባለፈው አንድ አመት ከሶስት ወር አጋርነታችሁን ላሳያችሁ በዛሬው ብይን ወቅትም ከፍተኛ ድጋፍ ስትሰጡን ለነበራችሁ የዞን9 ነዋርያን ከፍ ያለ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡

Saturday, July 18, 2015

ቁዘማ፤ ከዐቃቤ ሕግ ማስረጃዎች ብይን በፊት

 በፍቃዱ ዘ ሃይሉ
‹‹ስድስት መሥመር ስጡኝ፣
በታላቅ ፀሐፊ ከተጻፈ ድርሰት፤
አላጣም ምክንያት፣
አንዳች እክል ስህተት፣
ያንን ሰው ወንጅዬው የማሰቅልበት፡፡››
‹‹ለምን እፅፋለሁ?››
ጆርጅ ኦርዌል ‹‹ገንዘብ ለማግኘት›› ከሚደረግ ጥረት ውጪ ጸሐፍት የሚጽፉባቸውን ‹‹አራት ትላልቅ መግፍኤዎችን›› እንደዘረዘረ አንድ መጽሐፍ ላይ አነበብኩ፡፡ እነዚህ ከተራ ጉራ (sheer Egoism) - ጎበዝ መስሎ ለመታየት፣ ስለራስ እንዲወራ፣ ወይም ከሞት በኋላ ለመታወስ ለመሳሰሉት ዒላማ፤ ለጥበባዊ ግብ (aesthetic enthusiasm) - ዋጋ የሚሰጡትንና ሰዎች እንዲሰሙት የሚፈልጉትን ነገር የማጋራት ጉጉት፤ ለታሪካዊ ጥቅም (historical impulse) - ስለታሪክ እውነቱን የመለየትና ለወደፊቱ የማስቀመጥ ግብ እና ለፖለቲካዊ ተግባር (Political purpose) - ዓለምን ወደ ሚፈልጉት አቅጣጫ የመግፋት ዒላማ የሚደረጉ የምኞት መጻፎች ናቸው፡፡
የእኔም የመጻፍ አባዜ (ልበለው?) ከእነዚህ ኦርዌል መግፍኤዎች አንዱ ወይም ከፊሉ ወይም ሁሉም ወይም ማንኛውም ሊሆን ይችላሉ፡፡ ወይም ደሞ ነብይ መኮንን በግጥም እንዳለው ‹‹ስለሚያመኝና መፃፍ ስለሚያክመኝ›› ይሆናል፡፡ እንድ ነገር ግን አምናለሁ፡፡ የቮልቴርን አፍ ተውሼ እምነቴን ልናገር:- "we can, by speech and pen, make men more enlightened and better." (በንግግር እና ብዕር ሰዎች የነቁና የተሻሉ እንዲሆኑ ማድረግ እንችላለን፡፡)
ማዕከላዊእያለሁ የገባሁት ቃል ቢቆጠር ኖሮ መርማሪዎቼን ‹‹ፍቱኝ እንጂ ሁለተኛ አይለምደኝም›› ብዬ ለምኛቸው ነበር፡፡ መጻፍ ነውአይለምደኝምያልኩት፡፡ ልክ እንደልጅነቴ! ያኔ እናቴ ስትገርፈኝ እል እንደነበረው፡፡ ለምን እንደሆነ እንጃ እየተገረፍኩ የገባሁትን ቃል ያኔም፣አሁንም ማክበር አይሆንልኝም፡፡ ይኸው አሁንም እየጻፍኩ ነው፡፡ ይሄንኛው ለአንባቢ ከበቃ የማረሚያ ቤት ፈታሾች ሲሳይ ከሆኑት ቁዘማዎቼ ተነጥሎ ዕድል ገጥሞታል ማለት ነው፡፡
"It takes Power to talk to Power" (‹ጉልቤን ለማናገር ጉልቤ መሆን ያሻልእንደማለት) ይል ነበር አሉ ሳተናው ማልኮም ኤክስ፡፡ እኔና ጓደኞቼ ግን አፈሙዙን በአፈ-ብዕር ለማናገር ሞክረናል፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ታጋይ እያሉ ተስፋፅዮን መድኃንዬ(/) የተባሉ ኤርትራዊ ላሳተሙት Eritrea : dynamics of a national question መፅሐፍ የመልስ ምት ጽፈው ነበር፡፡ ተስፋጽዮንችግራችንን በሰላማዊ መንገድ እንፍታብለው በመጽሐፋቸው ሽፋን ገጽ ላይ በአፍጢሙ የተተከለ ጠብመንጃ (ከአበባ ጋር) በስዕል አስፍረው ነበር፡፡ አቶ መለስ በመልስ ምታቸው ‹‹ብረት ህዝቢ ኤርትራ ቁልቁል አፉ ኣይድፋእን›› ብለው አፈሙዟን ሽቅብ አቁመው ነፍስ ዘሩባት፡፡ የእሳቸው ትግል በአፈብዕርም፣ አፈሙዝም ነበር፡፡ አንደኛው ብቻ የሚገባቸው አይመስልም፡፡ ቁጭ ብዬ እየቆዘምኩ አስባለሁ፡፡ እንዳለመታደል (እንደመታደል) ሆኖ፣ ዛሬም፣ ከታሰርኩ ከአመት በኋላ የእርሳቸው ዓይነት ሌላኛው አማራጭ አይዋጥልኝም፡፡
የታሰርኩት በመጻፌ ነው፡፡ ዐቃቤ ሕግ ‹‹ይህ ሰው አሸባሪነው፤ የማሕረሰቡን ደህንነት አደጋ ላይ ጥሏል›› ብሎ ሲከሰኝ ያቀረበብኝ ማስረጃ ጽሑፎቼን ነው፡፡ ዐቃቤ ሕጉን ክሰስልኝ ያሉት ሰዎች ጽሑፎቼን በጽሑፍ ለመመከት ከመሞከር ይልቅ እንደመፍትሔ የታያቸው እኔን ዝም ለማሰኘት መሞከር ነው፡፡ ስለሚችሉ፡፡ አልፎ፣ አልፎ . . . የተከሰስኩባቸውን ጽሑፎች እመለከታቸዋለሁ፡፡ ‹‹መሰለፍ እና መሰየፍ ›› የሚል ርዕስ አያለሁ፡፡ ያላለቀ ጽሑፍ ነው፡፡ ሕዝቦቹን የማያምን መንግስት ሕዝቦች በሰላማዊ መንገድ ሲሰለፉ ሰይፉን ይመዛል ይላል፡፡ መቼም ሲያነቡት አይከሱኝም እላለሁ፡፡ አንዳንዱ ጽሑፍ እኔን ለመክሰስ ሳይሆን ለመከላከል ክሴ ላይ የተያያዘ ይመስለኛል፡፡ ሌሎቹን አነባለሁ፡፡ ‹‹80 ሚሊዮን እስከምንደርስ እንታገላለን ››ይላል፡፡ እንደ አምባገነኑ መንጌ ‹‹አንድ ጠመንጃ የሚል ተስፋ መቁረጥ አይነካካኝም›› ነው ነገሩ፡፡ ልዩነቱ የእኛ ትግል በብዕር ነው፡፡ 80 ሚሊዮን እኮ ሁላችንም ነን -እኛም፣ እንዲለወጡ የምንፈልጋቸው መሪዎቻችንም ተደምረን፡፡ ‹‹ድር ቢያብር ለአምባገነኖች ምናቸው ነው?›› የሚልም አለ (‹‹በሰገሌ ጊዜ›› ተጽፎ እኔም አንባቢዎቼም የረሳነው ጽሑፍ) ብዙዎቹ ማስረጃ የተባሉብኝ ጽሑፎች የተፃፉት ዞን ዘጠኝ ከመመስረቱ በፊት ነው፡፡ እውነት ግን ድር ቢያብር ለአምባገነኖች ምናቸው ነው? ‹‹አብዮት ወረት ነው›› የሚልና ሌሎችም አሉ፡፡ ሁሉም ግን ጽሑፎች ናቸው፡፡ በተጨማሪም ዞን ዘጠኝ ሲያደርጋቸው የነበሩ የብይነ መረብ ዘመቻዎች - ጋዜጣዊ መግለጫዎችም - የክሳቸን ማስረጃ ተብለዋል፡፡ ሕገ - መንግስቱ እንዲከበር ይጠይቃሉ፡፡
ያስከሰሱኝን ጽሑፎች ከጎኔ ለሚተኛው እስረኛ አስነበብኩት፡፡ ‹‹እንዴ፣ እንዴ . . . ›› አለ ገርሞት፡፡ ‹‹. . . ሁለት አመት ሙሉ መንግስት እንዴት ታገሳችሁ?›› የሕገ-መንግስታችንን አንቀጽ 29(ሐሳብን የመግለጽ ነፃነት) አነበብኩለት፡፡ ‹‹እሱ እኮ ኢሕአዴግ አይውጠው ነገር አምልጦት የተናገረው ነገር ነው፤ አንተ አምልጦህ የገባኸው ቃል፣ ቆይቶ ግን የሚፀፅትህ የለም?›› አለኝ፡፡ ለአልጋ ጎረቤቴ ከዚህ በላይ ላስረዳው አልሞከርኩም፡፡ ‹‹በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነበብኩት . . .›› የሚለው ተውሼ ያዋስኩትን ልቦለድ ነው፡፡ ባይረዳኝም እኔ እረዳዋለሁ፡፡
ለኔ መጻፍ መብት ብቻ ሳይሆን ግዴታም ነው፡፡ የሚያስገድደኝ አንዳች ጎትጓች ኃይል ውስጤ አለ፤ ይህንን ለእሱ ነግሬ ማሳመን አልችልም፡፡ ለነገሩ ለሌሎችም ነግሬ ማሳመን እየከበደኝ ነው፡፡ ‹‹አንተ የመንግስታቸንን ባሕሪ እያወቅከው ለምን ተዳፈርክ?›› ይሉኛል ችግሩ ከጽሑፌ ሳይሆን ከመንግስታችን መሆኑን የሚረዱት ዘመድ ወዳጆቼ ሳይቀሩ፡፡ዝም ብሎ የመኖርን ጥበብግን አይነግሩኝም፡፡ዝምታነዋ ቋንቋቸው! የባቢሎን ግምብ መሐላችን ቆሟል፡፡
‹‹
ብዙኃን ይመውዑ›› ይባላል፡፡ብዙኃንስ ይፈርዱብኝ ይሆን?› ይላል ልቤ፡፡ ምክንያቱም ልቤ በፍሬድሪክ ኒቼ አባባል ያምናል፡- "There are no facts, but interpretations." (ሐቅ ብሎ ነገር የለም፣ አተረጓጎም እንጂ)፡፡ ወዳጄ እና አባሪዬ አቤል ዋበላ ሁሌ ይሞግተኛል፤ ‹‹ነጭ ወይም ጥቁር (‹‹መላጣ››) እውነት ነው ያለው›› እያለ፡፡ እኔ ግን ‹‹እውነት ግራጫ ነች›› ባይ ነኝ፡፡ ይቺን ግራጫ እውነት እኔ ጽፌያት ብዙኃን ሲቀበሏት ነው የማይፈርዱብኝ፡፡ እውነቴ አይታያቸው ይሆናል፤ እኔግን አልቆጭም፡፡ ምክንያቱም፣ በቁዘማዬ መግቢያ አካባቢ እንዳልኩት ‹‹ብዕር ሰዎች ያነቃል›› ብዬ አምኜ ጽፌያለሁ፡፡ ብዕር ሁለት አፈሙዝ እንዳለው ሽጉጥ ነው፡፡ ተኳሹንም፣ ዒላማውንም ይመታል፡፡
በብዛት የጻፍኩት ራሴን ለማሳመን ስፍጨረጨር እግረ መንገዴን መሰሎቼን ለማሳመን ነው፡፡ ዒላማዬን ስቼ ብሆን እንኳ እራሴን አልሳትኩም፡፡ ዒላማዬን መሳትም ቢሆን የተኳሹ ድክመት ላይሆን የችላል፡፡ እጓለ ገብረ ዮሐንስ እንዳሉት ‹‹ጎልማሳ ጦርም ሆነ ሽመል አርቆ ይወረውራል፤ ዒላማውን ሳይመታ ቢቀር ከክንዱ መድከም ብቻ ሳይሆን ኢላማውም ወላዋይነት ሊሆን ይችላል፡፡››
መንግስታችን በኦርዌሊያን ፈሊጥ ነው የሚመራው (‹ሚ› ጠብቆ በይም ላልቶ ቢነበብ ግዴለም)፡፡ የወደፊቱን ለመቆጣጠር፣ አሁንን አጥብቆ ይዟል (እንደ ነብር ጭራ)፣ ያለፈውን ባሻው መንገድ ይተረጉማል፡፡ ለዚህ ግቡ መገናኛ ብዙኃን አንድም የእሱ ድምጽ የገደል ማሚቶ እንዲሆኑ አሊያም እንዲጠፉ ነው ምኞቱ፡፡ የእኔና የጓደኞቼ ምኞት ደግሞ ተቃራኒው ነበር ቢያንስ በማሕበራዊ ሚዲያ ላይ አማራጭ ድምፅ መሆን ተመኝተን ነበር፡፡ ለአማራጭ ድምፅነት የሰጠነው የተጋነነ ዋጋ በበኩሌ ኢ-ምክንያታዊ አይመስለኝም፡፡ ግራጫ እያልኩ የማጣቅሳት እውነት የምትወለደው ‹‹ጫፍ አልባ በሆነ›› የነጭ እና ጥቁር እውነቶች ፍጭት ነው፡፡ አማራጭ ቀለም ባይኖር ኖሮ የቀለሙን ዓይነት መጥራትም (መሰየምም) አያስፈልግም ነበር፡፡
ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት መንግስታችን ኦርዌሊያን ነው፡፡ ታሪክና ትርክትን መቆጣጠር ይፈልጋል፡፡ ያንን የሚያደርገው ደግሞ አንድም በብዕር (መገናኛ ብዙኃንን በመቆጣጠር)፣ አንድም በኃይል (አማራጭ ድምፃችንን በማፈን) ነው፡፡ ወቅቱ ከምርጫ 97 ማግስት ወዲህ ብዙ ጋዜጠኞችና ጸሐፍት የታሰሩበትና የተሰደዱበት ነው፡፡ እኔና ጓደኞቼም የዚሁ ዘመቻ ሰለባ ሆነናል፡፡ የታሰርነው ምርጫ 2007ን ምክንያት በማድረግ እንደሆነ ይገመታል፡፡አሁን ምርጫው ገዢው ፓርቲ በሚፈልገው መልኩ ተጠናቋል፡፡ ዳኞች የአቃቤ ሕጉን ማስረጃዎች መርምረው ውሳኔ ለመስጠት ለሐምሌ 13 ቀን ቆርጠዋል፡፡ ብዙዎች ይጠየቁኛል፤ ‹‹ምን እንጠብቅ?››
ሌሎች ምን መጠበቅ እንዳለባቸው ለመንገር ቀርቶ እኔ ራሴ ምን መጠበቅ እንዳለብኝ አላውቅም፡፡ የማውቀው ፍ/ቤቱ የሚወስነው ሳይሆን ለኔ(እና ጓደኞቼ) የሚገባንን ነው፡፡ ከነፃ በታች አያዋጣንም፡፡ ሆኖም ግን ሊሆን የማይገባው (ይሆናልና) ሆኖ ‹‹ጥፋተኛ›› ብንባልስ? መልሱን ከትልቅ ሰው አፍ ተንጠራርቼ እዋሳለሁ፡፡

‹‹የታህሳሱ ግርግር ›› በመባል የሚታወሰው የንጉሱ መፈንቅለ መንግስት እንደከሸፈ፣ ተሳታፊዎቹን የዳኙት ኖርዌያዊው ዳኛ ኤድቫርድ አምብሮ ጄኔራል መንግስቱ ንዋይ ላይ የሞት ቅጣት ሲበይኑባቸው ጄኔራሉ እንዲህ ነበር ያሉት፡- ውሳኔያችሁ ላይ ይግባኝ የለኝም፡፡ ፍትሕ የነፈጋችሁኝ ይህ ክስ ባግባቡ እንዳልከላከል ስታደርጉኝ ገና ነው፡፡ ያላችሁትን አድርጌያለሁ ፣ ግን ጥፋተኛ አደለሁም፡፡ ጽሑፍ እንደማስረጃ አቅርበው ‹‹አሸባሪ›› ነህ ካሉኝ፣ ከዚህ (ከጄኔራል መንግስቱንግግር) በላይ የማስተባብልበት አፍ የለኝም፡፡
BefeQadu Z Hailu