Thursday, September 10, 2015

የዞን 9 የ2007 ዓ/ም የእስር መስመር

የዞን 9 ጦማርያን ከታሰሩ አንድ አመት ከአምስት ወራት የተቆጠረ ሲሆን ወዳጅ ጋዜጠኞችን ጨምሮ ከጠቅላላው ዘጠኝ እስረኞች መካከል አራት ጦማርያን አሁንም በእስር ላይ በመሆናቸው ሁለተኛ እንቁጣጣሻቸውን በቅሊንጦ እስር ቤት ያከብራሉ ፡፡ ባለፉት አንድ አመት ከአምስት ወራት 36 ግዜ ፍርድ ቤት የተመላለሱ ሲሆን እስራቸው እና የፍርድ ሂደቱ በ2007 ዓ/ም ምን ይመስል እንደነበረ በመጠኑ እናያለን፡፡

የዞን 9 የእስር መስመር

መስከረም 2007  -የዓመቱ መጀመሪያ ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ በጻፈው  የቀድሞው አብዮተኛ ኑዛዜ  ተጀመረ፡፡ ጽሁፉ በአማርኛ እና በእንግሊዘኛ የዞን9 ጦማር ላይ ታትሟል፡፡

ጥቅምት 2007 የህግ የበላይነት እና ጸረ ሽብርህጉ ሲገመገም የሚለው ‹‹የጸረ ሽብር ሕጉና›› የአሁኗ ኢትዮጲያ ያላቸውን ግንኙነት አንዲሁም ምን ተፅእኖ እንዳለው የሚያሳየው ልዬ ሪፓርተዥ ተዘጋጀ፡፡
ጥቅምት 11 2007 ዓ/ም በእስር ላይ ይገኙ የነበሩትን ጦማሪት ማህሌት ፋንታሁንን እና ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬን የእስር ቤት አያያዝ አስመልክቶ የቀረበውን አቤቱታ ለማየት ችሎቱ ተሰየመ፡፡ በእለቱም እስር ቤቱ የተለየ አያያዝ መኖሩን ክዶ የተከራከረ ሲሆን ፍርድ ቤቱም አንደተለመደው እንዳይደገም በሚል የማረሚያ ቃል ችሎቱን አጠናቀቀው፡፡
ከጥቅምት 12 ጀምሮ ለአንድ ሳምንት የሚቆይ ለዞን9 ጦማርያን 6 ወር የእስር ቆይታን አስመልክቶ ለቤተሰቦቻቸውን ድካም የማገዝ የገንዘብ ማሰባሰብ ስራ በዞን9 ጦማርያን ወዳጆች አማካኝነት በተሳካ ሁኔታ ተከናወነ፡፡
ጥቅምት 25 - የዞን9 ጦማርያን ለአስረኛ ፍርድ ቤት ቀረቡ ፡፡

ህዳር 2007  -
ህዳር 1 ቀን የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ጠቅላይ ሚኒስተር ኃይማርያም ደሳለኝ በተለያዬ ሚዲያዎች ላይ ሲቀርቡ የሚሰጡትን አስተያየት ሕገ-መንግስታዊነትን የጣሰ መሆኑን አስመልክተው ደብዳቤ ጻፉ፡፡ ደብዳቤው የተከሳሾችን በህግ ፊት ንጹህ ሆኖ የመቆጠር መብት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እየጣሱ እንደሆነ እና እንዲታረም የሚጠይቅ ነበር፡፡
ሕዳር 3  ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞቹ ለ11ኛ ፍርድ ቤት ቀረቡ ፡፡ በዚህ የፍርድ ቤት ውሎም አቃቤ ህግ በአምስት ጉዳዬች ላይ ክሱን አንዲያሻሽል ትእዛዝ ተሰጠው ፡፡ ( ሊፈጽሙ ነው የተባለውን የሽብር ወንጀል በግልጽ ማስቀመጥ፣ ቡድኑ እየተባለ የተቀመጠው ቡድን ማን እነደሆነ በግልጽ ማስቀመጥ፣ የሥራ ክፍፍልን አስመልክቶ የተጠቀሰውን በግልጽ መስቀመጥ ፣ ተላከ የተባለውን 48000 ብር አስልክቶ በግልጽ ከማን አንደተላከ ማስቀመጥ ፣ ስልጠና የተባሉት ምን እንደሆኑ በግልጽ ማስቀመጥ እና የሽብር ስልጠና ሰጪ ድርጅቱን በግልጽ ማስቀመጥ ይገኙበታል)
ሕዳር 17 - በጦማርያኑ የዋስትና መብትን አስመልክቶ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት የቀረበው ይግባኝ ውድቅ ተደርጎ በእስር መቆየታቸው እርግጥ ሆነ ፡፡
ሕዳር 24 - ተሻሻለ የተባለው ክስ በድጋሚ ለፍርድ ቤት ቀረበ ፡፡ ጠበቆች የተሻሻለው ክስ ላይ አስተያየታቸውን አንዲሰጡ ተነገራቸው፡፡ ተሻሻለ የተባለው ክስ ቡድኑ ግንቦት 7 ነው ከማለት ውጪ ምንም አይነት መሻሻል ሳይደረግበት ነበር ለፍርድ ቤት የቀረበው ፡፡

ታህሳስ 2007
ታህሳስ 7 - ጦማሪ ዘላለም ክብረት በእንግሊዘኛ የጻፈው የናፍቆት ደብዳቤ  ታተመ
ታህሳስ 9 - ጦማሪ አቤል ዋበላ ‹‹ሕልም እንደሆነ አይታሰርም›› የሚለው ተወዳጅ ጽሁፉ በዞን9 ጦማር ላይ ታተመ ፡፡
ታህሳስ 27 ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞቹ በድጋሚ ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡ ፍርድ ቤቱ ክሱ አንዲሻሻል ታዞ ነገር ግን በተለያዩ አራት ጉዳዮች ላይ አሁንም ባለመሻሻሉ በድጋሚ አንዲሻሻል ሁለተኛ ትእዛዛ ሰጠ፡፡

ጥር 2007
ጥር 6 የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኛ ወዳጆች በድጋሚ ፍርድ ቤት ቀረቡ ፡፡ በእለቱ አቃቤ ህግ በድጋሚ አሻሻልኩት ያለውን ክስ ይዞ ቀረበ፡፡
ጥር 20 - ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ያቀረበውን ያልተሻሻለ ክስ እንደተሻሻለ መቁጠሩን በመግለጽ ተከሳሾች የህብረተሰቡን ደህንነት ወይም ጤና በማወክ በጸረ ሽብር ህጉ አንቀጽ 4 መከሰሳቸውን አጸና፡፡ የወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ የተጠቀሰበትን አንቀጽ በቀደመው ብይን ውድቅ በማድረጉም የተከሳሾች ጉዳይ ‹‹በጸረ ሽብር›› ሕግ ብቻ እንዲዳኝ ተወሰነ፡፡ የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ተቀጠረ፡፡
ጥር 26 - የዞን9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች በድጋሚ ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡ ፍርድ ቤቱ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ከመስጠታቸው በፊት መሃል ዳኛው አንዲነሱላቸው አቤቱታ አቀረቡ፡፡ ችሎቱም አቤቱታውን ሰምቶ ለመወሰን ሌላ ቀጠሮ ተሰጠ፡፡
ጥር 27 - በዚህም ቀጠሮ የተገኙት ተከሳሾች ሁለቱ ዳኞች ተሟልተው የዳኛው ይቀየርልን አቤቱታን መስማት ስላልቻሉ  በማግስቱ ለጥር 28 ተቀጠሩ ፡፡
ጥር 28 - በዚሁ እለት መሃል ዳኛው ባልተገኙበት ሁለቱ ዳኞች ጉዳዩን አይተው መሃል ዳኛው በፍርድ ሂደቱ ወቅት ጣልቃ አልገቡም አንዲሁም አፋጣኝ ፍትህን አላጓደሉም በማለት ውሳኔ መስጠታቸው ተገለጸ፡፡ ይህንን ተከትሎ የመሃል ዳኛው ምንም አንኳን በጉዳዩ ላይ ዳኞች ችሎቱ ላይ አንድቀጥል ቢፈልጉም ለእኔ ግን አንዲህ እየተባል ክሱ ላይ መቆየት አግባብ ስለማይሆን ራሴን ከችሎቱ አግልያለሁ በማለት አስተያየታቸው ሰጡ ፡፡ ( ነገር ግን ችሎቱን አሁንም የሚያስችሉት እኚሁ ዳኛ ናቸው) ፡፡
በተመሳሳይ እለት ጦማሪ አቤል ዋበላ ከማረሚያ ቤት የደረሰበትን የመብት ጥሰት ( በውሻ ሰንሰለት ታስሮ መቀመጥ እና በማዕከላዊ ሳለ በደረሰበት ድብደባ እንዲጠቀም የተገደደውን የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያውን መቀማት) አስመልክቶ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ አቀረበ ፡፡ ይህን አቤቱታውን በጽሁፍ አንዲያቀርብ ከፍርድ ቤት ቢነገረውም በእለቱ የነበረው ሂደት ብዙዎን በፍርድ ቤት ውስጥ እንባ አራጨ፡፡ በእለቱ የነበሩት የእስር ቤት ተጠሪ የማውቀው ጉዳይ የለም በማለት የመብት ጥሰቱን ክደዋል፡፡

የካቲት 2007
የካቲት 11 - የዳኛው መቀየር አቤቱታን ፍርድ ቤቱ ውድቅ ካደረገው በኋላ የዞን 9 ጦማርያ እና ጋዜጠኞች የካቲት 11 ቀን ለ20ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት በመገኘት የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ በእለቱን ጦማሪ በፍቃዱ ‹‹የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም ሽብር ተፈጽሞብኛል›› ሲል፣ ጦማሪ ናትናኤል በበኩሉ ‹‹እዚህ አገር ፍትህ ቢኖር ኖሮ እኔ የቆምኩበት ቦታ ላይ መቆም የሚገባቸው ከሳሾቼ ናቸው፤ ምንም አይነት ወንጀል አልፈጸምኩም›› የሚል ቃሉን ሰጥታል፡፡ ጦማሪ አጥናፍ ‹‹ምንም አይነት ወንጀል አልፈጸምኩም›› ያለ ሲሆን ጦማሪ አቤል በበኩሉ ‹‹የኅብረተሰቡን ደህንነት ለመጉዳት አላቀድኩም ለሽብር ተግባርም አላሴርኩም ብሏል፡፡››  የሴት እስረኞችን አያያዝ አስመልክቶ አጭር ቀጠሮ የሰጠን ሲሆን አጠቃላይ የማስረጃ ማሰማት ሂደቱን ግን ከአንድ ወር ከ10 ቀን በኋላ በተከታታይ ለሶስት ቀን ቀጥሮታል፡፡
የካቲት 18 - የሴት እስረኞችን አያያዝ አስመልክቶ ችሎቱ የተሰየመ  ጉዳዬን ለማየት በድጋሚ ቀጠሮ ሰጥታል፡፡  

መጋቢት 2007
መጋቢት 21 - የሰው ምስክር ናቸው ተብለው የቀረቡ ሰዎችን ምስክርነት መስማት ተጀመረ ፡፡ ሁሉም ምስክሮች እቃዎች ሲፈተሹ ያየን ነን በማለት የተያዙ እቃዎቸን ከማየታቸው በስተቀር ያቀረቡት የተለየ የወንጀል ምስክርነት አልነበረም ፡፡ ምስክሮቹ ተከሳሾን መለየት ሲያቅታቸው የተስተዋሉ ሲሆን በመጀመሪያው ቀን 6 ሰዎች ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ የተከሳሽ ጠበቆች ባልተካደ ነገር ላይ የፍርድ ቤቱም የተከሳሾችም ጊዜ መባከን አይገባውም እቃውም የእኛ አይደለም የሚል ቃል አልሰጠንም ስለዚህ የደረጃ ምስክሮች መስማት ይቁም ቢሉም ፍርድ ቤቱ ታዛቢዎቹን መስማት መቀጠል አለበት በማለቱ የተገኙ እቃዎችን ሲዘረዝሩ ከርመዋል ( መጽኃፍት ፣ መጽሄቶች፣ አርቲክሎች ላፕ ቶፕ ስልኮች እና ሲምካርዶች የመሳሰሉት ከፍተሻ ዝርዝሩ ውስጥ የተገኙ ናቸው)
መጋቢት 22 - ተጨማሪ 8 ምስክሮች በተመሳሳይ ሁኔታ ቃላቸውን ሲሰጡ ውለዋል፡፡ ከነዚህ በላይ ምስክሮችን ማቅረብ ያልቻለው አቃቤ ህግ ተጨማሪ ጊዜ በመጠየቁ ለመጋቢት 30 ቀጠሮ ተሰጥታል፡፡
መጋቢት 30 - አቃቤ ህግ ምስክሮቼ ጠፍተውብኛል፡፡ የሲዲ ማስረጃዎችንም የያዘው ሰው በአገር ውስጥ ስለማይገኝ ተጨማሪ ጊዜ ይሰጠኝ የሚል ጥያቄ አቅርቦ በመፈቀዱ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶ ችሎቱ ተበትናል ፡፡
መጋቢት 25 - ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ይድረስ ለኢቢሲ ጋዜጠኞች የጻፈው ጽሁፍ ታትሞ ወጥቷል፡፡

ሚያዝያ 2007
ሚያዝያ 16-19  የ6ቱ ጦማርያንን እና የ3ቱን ጋዜጠኞች እስር አንደኛ አመት አስመልክቶ ለነጻነታቸው ዋጋ የሚከፍሉትን እናወድስ የሚል የሁለት ቀናት ማስታወሻ ተዘጋጀ፡፡ በማስታወሻው ጦማርያኑ እና ጋዜጠኞቹ የደረሰባቸውን የመብት ጥሰት ዝርዝር እና የተያዙበትን እለት የነበረውን ድባብ ያሳየ ሲሆን ከ3 ሺህ በላይ ሰዎች በሁነቱ ላይ ተሳታፊ ሆነዋል ፡፡  በዚሁ የማስታወሻ ዝግጅት ላይ የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የላኩት የአንደኛ አመት ማስታወሻም ተስተናግዷል፡፡

ግንቦት 2007
ግንቦት 2
በዞን 9 ወዳጆች አማካኝነት የተዘጋጀው ሁለተኛው የቤተሰቦቻቸውን ሸክም መጋራት የሚለው የአንድ ሳምንት ዘመቻ ለሁለተኛ ጊዜ ተካሄዷል፡፡
ግንቦት19-21 በነዚህ ቀናት በዋለው ችሎት ላይ ከፍተኛ መወዛገብ ያሳየው አቃቤ ህግ ሲዲዎቹን እንደማስረጃ ማስመዝገብ ባለመቻሉ እና ምስክሮችንም ማቅረብ ስላልቻለ ሲዲዎቹ ከማስረጃ ላይ አንዲወገዱ እንዲሁም ተጨማሪ ምስክሮችን ለማቅረብም የተወሰነው ጊዜ በቂ ሆኖ አልተጠቀመበትም በሚል ምክንያት ተጨማሪ እድል እንዳይሰጠው ተወስኗል ፡፡
አቃቤ ህግ አንደኛ ተከሳሽ ሶልያና ሽመልስ ላይ አለኝ ያለውን የሲዲ ማስረጃ አስመልክቶ ሌሎች ተከሳሾች ማየት አለባቸው ወይስ ፍር ቤቱ በጽህፈት ቤት ማየት አለበት የሚለውን ለመወሰን ሰኔ 8 ተቀጥሯል፡፡
በተመሳሳይ ቀን ችሎት ውስጥ አቤል ዋበላ ከዳኞች ጋር በነበረው አለመስማማት የተነሳ የችሎት መድፈር ጥፋተኛ ተብሎ ለቅጣት ለግንቦት 25 ተቀጠረ፡፡
ግንቦት 23 - ሥነ-ስርዓት የሚለው የጦማሪ አቤል ዋበላ ጽሁፍ ታትሟል፡፡
ግንቦት 25 አቤል ዋበላ በችሎት መድፈር በገደብ 4 ወር ተፈርዶበታል ፡፡

ሰኔ 2007
ሰኔ 8 - ፍርድ ቤት የቀረቡት 9 ተከሳሾች  ከብይን ለሃምሌ 13 የተቀጠሩ ፡፡ በእለቱም አንደኛ ተከሳሽ ላይ የቀረበውን የሲዲ ማስረጃ በጽህፈት ቤት አይተን እንደማስረጃ ቆጥረነዋል፡፡ ለሌሎች ተከሳሾም መድረስ አይገባውም በማለት ችሎቱ ወሰነ

ሃምሌ 2007
ሃምሌ 1 ቀን 2007 ዓ/ም ባተጠበቀ ሁኔታ ሶስቱ ጋዜጠኞች እና ሁለት የዞን9 ጦማርያን ክሳቸው ተቋርጦ ከእስር መፈታታቸው ዜና ተሰማ ፡፡ በእለቱ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ፣ ጋዜጠኛ አስማማው ሃይለጊዮርጊስ እና ጦማሪ ዘላለም ክብረት ሲፈቱ በማግስቱ ጠዋት ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ እና ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁን ተፈቱ፡፡





በተመሳሳይ ቀን በቀሪዎቹ 5ቱ ተከሳሾች ላይ ክሱ አንደሚቀጥል የመንግስት ወዳጅ የሆነው ሬዲዬ ፋና በድረ ገጹ አሳወቀ ፡፡
ሃምሌ 9-11 ለሶስት ቀናት የሚቆይ እስቲ አንነጋገር የማስረጃን ነገር በሚል የተዘጋጀው ዘመቻ ተካሄደ ፡፡ ይህ ዘመቻ ሃሳቡ ተከሳሾች ላይ ማስረጃ ተብለው የቀረቡ ጉዳዬችን ለአደባባይ ማብቃትና ቀሪ አራት ታሳሪዎች የሚከላከሉት ምንም ነገር እንደሌለ ለማሳወቅ የታለመ ነበር ፡፡
ሃምሌ 10 - ጦማሪ በፍቃዱ ቁዘማ፣ ከአቃቤ ሕግ ማስረጃዎች በፊት እና ጦማሪ ናትናኤል የዕለት ተዕለት ጥያቄዎቻችን ብይናቸውን አስመልክቶ የጻፋቸው ጽሁፎች ታተሙ፡፡
ሃምሌ 13 - ፍርድ ቤቱ የአንድ ምስክር ቃል ተገልብጦ አልደረሰኝም በማለት ብይኑን መስራት አለመቻሉን ገልጾ ጽሁፉ መገልበጡን ለማረጋገጥ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጠ ፡፡
ሃምሌ 22 - የተከሳሾች ጽሁፍ ተገልብጦ ማለቁን አረጋግጫለሁ ያለው ፍርድ ቤቱ ከጽህፈት ቤት በማስቻል በድጋሚ ለጷጉሜ 2 ቀጠሮ ሰጠ
ሃምሌ 25 - ጥቂት ስለማእከላዊ የሚል ጽሁፍ ታተመ፡፡

ሜ 2007

በአመቱ የመጨረሻ ሳምንት የመጨረሻ የእስር ሳምንታቸው ይሆናል ተብሎ ተስፋ ቢደረግም ፍርድ ቤቱ ዳኞች አልተሟሉም በሚል ሌላ ሰበብ ሁለተኛ እንቁጣጣሻቸውን በእስር እንደሚያሳልፉ ያረጋገጠውን የ31 ቀን ቀጠሮ በመስጠት ለመስከረም 27 ለአራተኛ ጊዜ በአጠቃላይ ደሞ ለ37ተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጠ ፡፡ 

5 comments:

  1. 1.嘎志 毘嘎志 若喀 札夏 嘛尼 梭哈

    2.唵 班雜 別噶 札嘛 吽

    3.達列 達列 達阿呀 拔噶哇爹 邊達摩雜餒 梭哈

    4.那摩拔噶哇爹 悟尼卡牙 達列 達仁爹耶梭哈

    5.爹呀他 班扎 班扎 嘛哈班扎 薩哇 巴呀地 哈那 哈那 班扎那梭哈

    6.唵 沙瓦尼瓦那 比堪匹尼 吽吽呸

    7.唵 自松 自松 梭哈

    8.嘿 嘿 拉尤 拔大呀

    9.唵 薩哇 作拉 踏讓咩 吽梭哈

    10.那摩 拔噶哇爹 悟尼卡牙 達列 讓爹 梭哈

    11.唵 拔噶哇爹 休地密日(字)地 拔拉 拔拉 哇 阿麻 悉地梭哈

    12.爹呀他 卡利 卡利 拔利爹 梭哈 爹呀他 嘎哇匝 噶那 阿拉爹 梭哈

    13.唵 阿必惹 吽 嘎雜那 (唵 嘎貝那嘎母娑哈)

    14.oṃ maṇi padme hūṃ

    15.Ah Ah Sha Sa Ma Ha

    16.ong pu long suo ha

    17.爹呀他唵貝喀則也貝喀則也

    18.爹呀他唵牟尼牟尼嘛哈牟尼 釋迦牟尼耶梭哈

    19.唵訶訶訶尾娑摩曳娑婆賀

    20.爹欣谢巴悉吉艾巴南巴嫩巴拉洽擦洛

    ReplyDelete