Wednesday, October 15, 2014

የዞን9 ጦማርያኑ እና የወዳጅ ጋዜጠኞች የፍርድ ቤት ውሎ

 #FreeZone9bloggers #Ethiopia

የዞን9 ጦማርያኑ እና የወዳጅ ጋዜጠኞች የፍርድ ቤት ውሎ

ከሁለት ወር ቆይታ በኋላ በነሶልያና ሽመልስ የሽብር ወንጀል የክስ መዝገብ ልደታ ፍርድ ቤት የቀረቡት ስድስቱ የዞን9 ጦማርያን እና ሶስቱ ጋዜጠኞች ቀጠሮ ችሎቱ ከ20 ቀን በኃላ እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ በመስጠት ተጠናቀቀ። 

ፍርድ ቤቱ በዛሬው ውሎው የተከሳሽ ጠበቆች ክሱ ላይ ያቀረቡትን የክስ መቃወሚያ አቃቤ ህግ አይቶ ምላሽ እንዲሰጥበት የተቀጠረ ሲሆን በዚያም መሰረት ለተከሳሽ ጠበቆች የክስ መቃወሚያ አቃቤ ህግ የፅሁፍ ምላሽ ሰጥቷል ። 

ፍርድ ቤቱም የጠበቆችን የክስ መቃወሚያ እና የአቃቤ ህግን ምላሽ መርምሮ በክሱ ሂደት ላይ ብይን ለመስጠት ለተጨማሪ ሃያ ቀን ለጥቅምት 25 ቀጠሮ ሰጥቷል። 

በተጨማሪም የሴት ተከሳሾችን በጓደኛና በቤተሰብ አለመጎብኘት ተከትሎ ያቀረቡትን አቤቱታ እንዲያስረዳ የማረሚያ ቤቱ እንዲገኝ ጥሪ ቢደረግም አለመገኘቱን እና በፓሊስ በኩል ምላሽ ይዞ መቅረቡን ተከትሎ ፍርድ ቤቱ በሚቀጥለው ቀጠሮ የማረሚያ ቤቱ ሃላፌ እንዲገኙ ትእዛዝ አስተላልፎ ነበር። ነገር ግን ሴት ተከሳሾች በተለይ ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳየ የመጎብኘት መብት መሰረታዊ መብታቸው በመሆኑ 20 መቆየት እንደማይገባ በመጠየቃቸው ፍርድ ቤቱ የሴት ተከሳሾችን የጉብኝት መብት አስመልክቶ ለማየት ለጥቅምት 11 አጭር ቀጠሮ ሠጥቷል ። 

በዛሬው እለት ነጭ በመልበስ የተገኙት ተከሳሾች በመልካም ፈገግታ እና በጠንካራ መንፈስ የነበሩ ሲሆን በፈገግታ ወዳጅ እና ጓደኞቻቸውን ሰላም ሲሉ ተስተውለዋል። 

በመጨረሻም የሚቀጥለው ቀጠሮ ለጥቅምት 25 የተወሰነ ሲሆን የሴት ታሳሪዎችን የጉብኝት መብት ጥያቄ አስመልክቶ በጥቅምት 11 ችሎቱ ቀድሞ ይሰየማል ተብሎ ይጠበቃል።

የዞን9 ጦማርያን የክሱን ፈጠራነት፣ የጦማርያኑን እና ጋዜጠኞቹ በመአከላዊ ምርመራ ያለፉበትን የመብት ጥሰት እያስታወስን የፍትህ ስርአቱ የሚታማበትን የፓለቲካ መጠቀሚያነት ክስ ወዳጅ ጋዜጠኞችን እና ተከሳሽ ጦማርያንን በነፃ በማሰናበት ፍርድ ቤቱ ይህንን ታሪካዊ አጋጣሚ እንደሚጠቀምበት ተስፋ እናደርጋለን።

No comments:

Post a Comment