Monday, July 29, 2013

ኢትዮጵያዊው ዳያስፖራ


በታዬ ዘሐዋሳ

በሃገራችን በነበረው ፖለቲካዊ ቀውስ ወይም አመለካከት የተነሳ በርካታ ኢትዮጵያውያን በስደት እንደሚኖሩ ይታወቃል:: የሚኖሩበትም ሃገር ብዛትና ስብጥር በራሱ ከሌሎች ሃገራት ዜጎች የተለየን ያደርገናል ብዬ አስባለሁ:: እንደ ሃገራቱ ስብጥር እና ብዛት ሁሉ የሃበሻ አመለካከትም እጅግ ብዙ ነው:: ይህ ብዛት ያለው ስብጥር ደግሞ ወጥ የሆነ አመለካከት እንዳይኖረን አድርጓል:: ክፍፍላችንም እንደዚያው ብዙ ነው:: ፍረጃችንም ጭምር:: የዛኑ ያክልም ኢትዮጵያዊ ዳያስፖራ ለመፈራረጅ ወይም ለመሞጋገስ ከንፋስ የፈጠነ ነው:: ፍረጃው ከተለያዩ አካላት ይጀመር እንጂ አብዛኛዎቹን ፍረጃዎች በማዳነቅና በማሟሟቅ ረገድ የሁሉም ድርሻ አለበት:: አንዲት የፌስቡክ ወዳጅ ስለፍረጃዎች ብዛት እና ጥልቀት ትዝብቷን አካፍላን ነበር:: ከነዚህ የርስ በርስ ፍረጃዎች ውስጥ የሚከተሉት በስፋት የምናስተውላቸው ናቸው:-

 . ኢቲቪ ወይም ኢሳት
 . ኢህአዴግ ወይም ተቃዋሚ
. አይጋ ፎረም ወይም ኢትዮጲያን ሪቪው
. አዲስ ዘመን ወይም ፍትህ
. ኢትዮጲያ ወይም ሞት ወይም ገንጣይ ተገንጣይ
. እምየ ሚኒሊክ ወይም አፄ ዮሃንስ
. ኢትዮጲያ ፈርስት ወይም ኦሮሞ ፈርስት
. ልማት ወይም ሰብአዊ መብት
. ንኡስ ከበርቴ ወይም ደሃ
. ኪራይ ሰብሳቢ ወይም ልማታዊ
. ሰለፊስት ወይም አህባሽ
. የውጪ ሲኖዶስ ወይም የሃገር ውስጥ ሲኖዶስ
. የምርጫ ትግል ወይም የትጥቅ ትግል
. ጠባብ ወይም አገር ወዳድ
. ባንዳ ወይም ጀግና
. የባንዳ ልጅ ወይም የጀግና ልጅ
. X ወይም Y እያለ ይቀጥላል::

ይህን የፍረጃ ብዛት እና አይነት ለግዜው በዚህ እናብቃው:: የፅሁፌ መነሻ ርዕሥ በርካታ ሃሳቦችን ማስነሳት እንዲሁም ኢትዮጵያዊ ዳያስፖራን በተመለከተ የተለያዩ ሃሳቦችን ማንሳትና ማወያየት እንደሚችል ግልፅ ነው:: አነሰም በዛም እነዚህን ሃሳቦች እያነሱ መወያየትም ሆነ መተራረም ስለ ድክመታችን አውቀን የማስተካከያ እርምጃ እንድንወስድ ይረዳናል:: ድክመቱን በገደምዳሜ እያየን የምናልፈው ከሆነ ግን ለሃገራችንም ሆነ ለህዝባችን ፋይዳ አናመጣም:: መፅሃፉ እንዳለውም አስቀድሞ በአይናችን ያለውን ምሰሶ ማውጣት ስንችል ነው የጓደኛችንን ጉድፍ ማየት የምንችለው:: ነገር ግን የኛ ዳያስፖራ እሱ ያለው እንጂ ሌላው የሚለው ትክክል አይደለም ብሎ የማሰብ አዝማሚያ ያሳያል:: እናም ምናልባት የኔ ሃሳቦች ከተወደደው ዳያስፖራ ሃሳብ ጋር ካልተስማሙ የማይስማሙበትን ሁኔታ ለመስማት ዝግጁ መሆኔን አስቀድሜ ልግለፅ:: የባህርያችንን ጥልቀት ለማሳየትም ይመስላል "ኢትዮጵያ የገባ አንድ ፀሃፊ በማግስቱ ስለ ኢትዮጵያውያን ከአንድ በላይ መፅሃፍ ሊፅፍ ይችላል:: በሁለተኛው ቀን ምናልባት ከተሳካለት ለጋዜጣ የሚሆን መጣጥፍ ሊፅፍ ይችላል:: ሳምንት ሲቆይ ግን ሰው ስለ ኢትዮጵያውያን አንድ አረፍተ ነገር እንኳ መፃፍ አይችልም" አለ የሚባለው:: ለማንኛውም ለዛሬ የሚከተሉትን "እዛም እዛም የረገጡ" ሃሳቦችን ላንሳ:: ነገር ግን የማነሳቸው ሃሳቦች ከጥቂት ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች ጋር ግንኙነት የሌላቸው እና እንደማይመለከታቸውም ባውቅም ብዙሃኑን ይወክል ዘንድ እነዚያን ጥቂቶችም የፅሁፌ አካል አድርጌያቸዋለሁ:: ለዚህ አስቀድሜ ይቅርታ እጠይቃለሁ::

Friday, July 19, 2013

የስደተኛው ማስታወሻ ከአውሮጳ


(ክፍል ፭)

ውዴ:-

ባለፈው ከሳሚ ጋር ስለመጠለያ ጣቢያ ስንጨዋወት ስሙን መቀየር ስላልፈለገው ጓደኛቸው ያጫወተኝን እየነገርኩሽ ነበር ያቆምነው፡፡የሳሚ ታሪክ ይህንን ይመስላል፡፡ እሱን አንብቢና ስደተኛ በአውሮፓ የሚጠብቀውን ህይወት ገምቺ፡፡
 
ከዚያ
ጊዚያዊ ካምፕ የመቆያዬን ጊዜ ጨርሼ ወደተመደብኩበት ቋሚ መኖርያ ስሄድ ካገሬ ሥሰደድ ያልተሸኘሁትን አይነት ሽኝት በዚያ ካምፕ ባገኘኋቸው ወገኖቼ ተደረገልኝ። በውድቅት ሌሊት የምሔድበት መኪና የሚቆምበት ቦታ ድረስ መጥተው መልካም ምኞታቸውን ገለጡልኝ። እኔም አፀፋውን መለስኩና ወደዚያ ከተማ ሄድኩ። ከነዚህ የአጭር ጊዜ ወዳጆቼ ጋር እስከአሁን እንደዋወላለን። ወዴት እንደሄዱ ሳላውቅ ደብዛቸው የጠፉም ሞልተዋል።

ከትልቁ ጊዚያዊ መጠለያ ወደዚያ ስንሄድ አንድ አበሻ ብቻ ነበር የማውቀው። እሱም ከኔው ጋር ተመድቦ በአንድ ባቡር አብሮኝ የነበረ ነው። እዚያ የደረስነው ጥር አጋማሽ ላይ ስለነበር የነበረው አየር እጅግ ይገርም ነበር። መሬት የሚባል ነገር አይታይም። በሙሉ ነጭ ነው፣ ዛፉም የእግዜር ስሪት አይመስልም፣ ከመንጣቱና ከቅርፁ የተነሳ ሰውሰራሽ ይመስላል። ብርዱ ለመግለፅ በሚያስቸግር መልኩ ተስፋ ያስቆርጣል።

ከባቡር እንደወረድን የመጠለያው ሰራተኞች ፎቷችን ያለበትን ወረቀት ይዘው ስለነበር ገና ከደረጃው ስንወርድ በስማችን እየጠሩ ተቀበሉን። ወደውጭ ባየሁት ነጭ መልክዓምድርና የሚያቃጥል ቅዝቃዜ የተፈጠረብኝን ስጋት ለማርገብ ስለከተማውና ስለምንኖርበት ቦታ እየተርበተበርኩ እንደምንም ብዬ በምችላት ጥቂት እንግሊዝኛ መጠየቅ ጀመርኩ። ሁኔታዬን የተረዳው ሰራተኛምአይዞህ ሁሉም ሲመጣ እንዳንተው ይሆንና ትንሽ ሲቆይ ይለምደዋልአለኝ።

ከመኪናው አስገብቶን 30 ደቂቃ ነዳው። ግራ በመጋባት አብሮኝ ካለው ልጅ ጋር ተያየን። ወዴት ነው የምትወስደን ብለን ጠየቅነው።እዚሁ ነው! የናንተ መጠለያ  ከከተማው ወጣ ይላል፣ አይዟችሁ ባካባቢው የሚኖር ማሕበረሰብ ስላለ የገበያ ችግር የለምአለን።