Wednesday, June 26, 2013

#ስንፍና፤ ባሕላችን ነው እንዴ?



ሁሉም ሰው የለውጥ ምኞት አለው፣ ሁሉም ሰው የለውጥ ምኞቱን እውን ማድረግ የሚችልባቸውን አማራጮች ከሞላ ጎደል ያውቃቸዋል፣ ሁሉም ሰው ግን ለውጡን እውን የማድረግ አቅም የለውም፡፡ ጥቂቶች ናቸው ይህንን ማድረግ የሚችሉት፡፡ ዋነኛው ምክንያታቸው ደግሞ ስንፍና ነው፡፡ የስንፍና ተቃራኒው ጉብዝና ነው እንበልና - ጉብዝናቸውን ከስንፍናቸው ማስበለጥ የቻሉ ሰዎች ብቻ ለውጦችን ማስመዝገብ ይችላሉ ብለን መጣጥፉን በድምዳሜ እንጀምረው፡፡

ከላይ ‹ጉብዝናን ከስንፍና ስለማስበለጥ› ያወራኋትን ነገር ‹‹ለመግቢያ መግባቢያነት›› እንድደግማት ፍቀዱልኝ፡፡ ጉዳዩ አወዛጋቢ ቢሆንም ሰዎች ሁሉ በጥቅሉ /በመሠረታዊ ነገራቸው/ አንድ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ ጥልቀቱ እና ስፋቱ ይለያይ እንጂ፣ በትምህርትና በልምምድ ብሎም በኑሮ አጋጣሚ ይዳብር/ይሳሳ እንጂ ሁሉም በሰብኣዊነታቸው የሚጋሯቸው ባሕርያቶች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ ስንፍና እና ጉብዝናን ነው መርጬ ላወራበት የፈለግኩት - በተለይ ስንፍናን፡፡ ሆኖም በማወራበት ጊዜ ሁሉ ፍፁም ስንፍናን (ወይም ፍፁም ጉብዝናን) እያሰብኩ እንዳላወራሁ እንድትገነዘቡልኝ እፈልጋለሁ፤ የሌለውን ከየት አመጣዋለሁ?!

ስንፍና - የኢትዮጵያውያን ባሕል?

ይህንን ጽሑፍ ለመጻፍ ስነሳ ገና ‹‹ኢትዮጵያውያን የስንፍና ባሕል አለብን›› የሚል ስጋት እየተጫጫነኝ መሆኑን አልደብቃችሁም፡፡ ጥያቄው፤ ይህ ሰብኣዊ ባሕርይ ባሕል ሊሆን ይችላል ወይ? ባሕል ሊሆን የሚችል ከሆነስ ኢትዮጵያውያን ስንፍናን ባሕል አድርገውታል ወይ? ኢትዮጵያውያን ባሕል አድርገውታል/አላደረጉትም ለማለትስ ሁሉንም በአንድ መጨፍለቅ እንችላለን ወይ? (ለምሳሌ አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ ጉራጌው… ሁሉ በየራሱ የሥራ ባሕል ውስጥ የሚኖር ስለሆነ አንድ ዓይነት የስንፍና/ጉብዝና ባሕል ይኖረዋል ወይ? የክርስትያን ሙስሊሙስ የሥራ ባሕል አይለያይም ወይ?...)

ጥያቄዎቹን ባወጣሁ እና ባወረድኳቸው ቁጥር የመመለስ አቅሜ ውሱን እንደሆነ ተረድቻለሁ፤ ሆኖም ጥያቄውን ማንሳት በራሱ ወደመልሱ የሚያመራ ነውና መጻፌን አላቋረጥኩም፡፡

Tuesday, June 25, 2013

በጭቆናና በበደል የተፈተነ የፍትህ እና እኩልነት አባት - ዶ/ር ቢሂምራዎ ራምጂ አምበድከር

ክፍል ፩

በማናዬ በላይ
አምበድከር በኢኮኖሚክስ ለኔ አባቴ ነዉ፡፡ እሱ ማለት ከሰራዉ በላይ ምስጋና የሚገባዉ ለተጨቆኑ የኖረ ጀግና ነዉ፡፡ ምንም እንኳን ከእዉነት በራቀ ምክንያት በሀገሩ አወዛጋቢ ቢሆንም ለኢኮኖሚክስ እድገት ያደረገዉ አስተዋፅኦ ገራሚ እና ሁሌ ሲዘከር የሚኖር ነዉ፡፡
አማርትያ ሴን


I.        ቅድመ ታሪክ
    ከሰዓት ነዉ፤ በጠራራ ፀሀይ ከትምህርት የሚመለሰዉ ህፃን እጅጉን ዉሀ ተጠምቷል፡፡ በአካባቢዉ ወደሚገኙ ቤቶች ሄዶ ዉሀ ለመነ ማንም ዉሀ ለመስጠት ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ ይህ ህፃን በአቅራቢያ ወዳለዉ የዉሀ ታንከር በማምራት ዉሀዉን ለመክፈት ሲታገል ያዩት ነዋሪዎች ለልጅ በማይመጥን ፍልጥ ያሳርፉበታል፡፡ የዉሀ ጥም ጉሮሮዉን እንዳከሰለዉ ይህ ህፃን ጥቂት ኪሎሜትችን ተጉዞ  እቤቱ ይደርሳል፡፡ ለቤተሰቡ ያቀረበዉ የመጀመሪያ ጥያቄ ‹ለምን?› የሚል ነበር፡፡

    በሌላ ጊዜ ይህ ህፃን ከታላቅ ወንድሙ ጋር በመሆን ከሚማሩበት ቦታ ለስራ ተለይቷቸዉ ወደነበረዉ አባታቸዉ ለመሄድ ጋሪ ተሳፍረዉ እየሄዱ ሳለ በመሀል ጋሪዉን የሚዘዉረዉ ካስት ሂንዱ የእነዚህ ህፃናት ማንነት ከተረዳ በኋላ ለህፃናቱ ለነሱም እንግዳ በሆነ እና በማያዉቁት ምክንያት ጋሪዉ እየከነፈ ገፍትሮ መሀል ሜዳ ይጥላቸዋል፡፡ አሁንም ጥያቄያቸዉ ‹ለምን?› ነበር፡፡

    ሌላ ልጨምር ከትምህርት ቤት ወደ ቤቱ እየተመለሰ ያለዉ ህፃን በመሀል ዶፍ ዝናብ ይይዘዋል፡፡ ከዚህ ዝናብ ለመጠለል በመንገዱ ላይ ወደሚታዩት ቤቶች ይጠጋል፡፡ የህፃኑን ማንነት ያዉቁ የነበሩት ሰዎች ገና ከሩቅ እንዳይደርስ ይከለክሉታል፡፡ ክልከላዉን አልፎ ቢጠጋ ምን እንደሚደርስበት በዚች በለጋ እድሜዉ ያየዉ ፈተና አስተምሮታልና ዝናቡን መርጦ መንገዱን ይቀጥላል፡፡ እቤትም ሲደርስ የሚማርበት ደብተር እና መፃህፍት አንዳይሆን ሆነው ነበር፡፡

    የእንሰሳትን ፀጉር ሳይቀር የሚቆርጥ ፀጉር አስተካካይ የእርስዎን ፀጉር ቢፀየፍ፣ ትምህርት ቤት እንደሌላዉ ተማሪ ሳይሆን ከክፍል ዉጭ ሆነዉ እንዲያዳምጡ አሊያም ከአብዛኛዉ ተማሪ ተነጥለዉ በርቀት ማዳመጥ ብቻ ተፈቅዶሎት ቢማሩ ፤ ማንኛዉም የህዝብ አገልግሎት እርስዎን ቢያገል፣ ዉሀ በርቀት የሚያንቆረቁርልዎ ሌላ ሰዉ ከሌለ የዉሀ መጠጫዉን አሊያም ቧንቧዉን ነክተዉ መጠጣት ቢነፈጉ፣ በተወሰነ መንደር አቅራቢያ ማለፍ ቢከለከሉ፤ የሚያመልኩትን እምነት ምንነት ማወቅ ቢነፈጉ፤ በቤተ እምነቱም አይደለም መሄድ ጥላዎ እንኳን እንዳይደርስ ቢደረጉ ምን ይሰማዎት ይሆን?

    ከላይ የተገለፁትን ከፊሎቹ ሲሆኑ እነዚህን ተግባራት በተፃረረ መልኩ ለሚከዉኑት ተግባር የሚደርስብዎ ቅጣት ማኅበራዊ መገለል አሊያም መደብደብ ብቻ አይደለም ሐይማኖቱ ያዛል በሚሉት ኢ-ሰብአዊ ቅጣት ማሰቃየት ጭምር እንጂ፡፡ ለምሳሌ አንድ ሹድራ (የዝቅተኛ ካስት አባል ቬዳን (ቬዳ አንዱ የሂንዱ ሀይማኖታዊ መፅሐፍ ነዉ) ከተማረ ያዳመጠበት ጆሮ ዉስጥ የቀለጠ ሊድ በጆሮዉ እንዲንቆረቆር ያዛል፡፡ ይህም ሂንዱ ሐይማኖት ለአማኒዎቹ ስለ ሐይማኖቱ ምንነት እንዳያዉቁ በመከልከል በዓለማችን ብቸኛዉ ሀይማኖት ያደርገዋል፡፡

    በአጠቃላይ ይህ እንግዲህ ከጥቂት አስርት አመታት በፊት በ1950 እና 60ዎቹ ጭምር በሙሉ ህንድ የሚተገበር አፀያፊና አሳፋሪ የማኅበረሰብ ስደራ (የካስት ወይም ቻቱርቫርና) ስርዓት ነዉ፡፡

    Caste/Chaturvarna የሚለዉ ቃል Class ወይም መደብ ከሚለዉ ቃል ጋር የሚቀራረብ ቢመስልም ጠለቅ ብሎ ለተመለከተዉ ልዩነቱ የጎላ ነዉ፡፡ በህንድ ያለዉ ካስት ስርዓት የሚያመለክተዉ በደረጃ የተሰደረ ቀድሞ በዉልደት የሚታወቅ ማኅበራዊ ድልድል ሲሆን አንድዬ በዘር ካገኙት መግባትም ሆነ መዉጣት የማይቻልበት ወደላይ ክብርን እና አገልጋይነትን ወደታች ንቀትና ትዕቢትን የሚያሳዩበት ስርዓት ነዉ፡፡ ካስት ዘላለማዊ ሲሆን ክላስ በአብዛኛዉ ጊዜያዊ ነዉ፡፡ ለምሳሌ ድሀ ከሆኑ ሀብታም በሚሆኑበት ጊዜ የሀብታሙን መደብ ይቀላቀላሉ፡፡ ለዚህ ነዉ መደብ የሚለዉ ቃል ምሉዕ በሆነ ሁኔታ የህንድን ካስት ስለማይገልፀዉ ካስት የሚለዉን ቃል ለመጠቀም የመረጥኩት፡፡

    ዘርዎ ከላይኛዉ ከምሁሩ ከብራሐሚን ክፍል ከሆነ የእርስዎ ጨዋነት (አላዋቂነት) ብዙ አያሳስብዎትም በቃ ሲፈጥርዎ አዋቂ ነዎት ተብሎ ይታሰባል ሌሎችም እርስዎን ሊያገለግሉ ግድ ነዉ፡፡ በተቃራኒዉ የዝቅተኛዉ ሹድራ አባል ከሆኑ የእርስዎ የመጠቀ እዉቀት ለዉጥ አያመጣም የተፈጠሩት በጉልበት ለማገልገል ነዉና፡፡

    • የህንድ ካስት/ቻቱርቨርና ስርዓት


    በህንድ ቫርና አራት ካስት በፒራሚድ መልክ የተሰደረ ሲሆን ብርሀሚን ከፈጠሪዉ (ማኑ) ጭንቅላት የተሰሩ ናቸዉ ተብለዉ የሚታሰብ ሲሆን የተማሩና የሀይማኖት አገልጋዮች ናቸዉ፣ ሸትሪያስ ከእጅ የተሰሩ ወታደር ናቸዉ፤ ቫይሲያስ ከእግር የተሰሩ ነጋዴ፣ ገበሬ፣ እንስሳት የሚያረቡትን ሲጨምር የመጨረሻዉ ሹድራ ከአምላካቸዉ ጥፍር የተሰሩ ናቸዉ ተብሎ ስለሚታመን የጉልበት ሰራተኞች (አገልጋይ እንደማለት) እና የተናቁ ናቸዉ፡፡ ከላይ የተገለፀዉ ግፍ የሚደርሰዉ በዝቅተኛ ላይ በሚገኙት በህንድ በቁጥር አብላጫዉን በሚይዙት በሹድራ ማህበረሰብ ላይ ነዉ፡፡ የካስት ስርዓቱ በዚህ አያበቃም በየካስቱ ዉስጥም የተለያዩ ክፍፍሎች ያሉት ሲሆን ሹድራዉ ከሌላ ሹድራ ለምሳሌ መፀዳጃ ቤት የሚያፀዳዉ ከጫማ ሰሪዉ የተሻልኩኝ ነኝ ብሎ እንዲያስብ የተደረገ ተጨማሪ ድልድል ይመስላል፡፡

    በህንድ የካስት ስርዓት ከሚመስልዎ ካስት ጋር ካልሆነ በቀር ጋብቻ አሊያም ራት አብሮ መመገብ ሲያምሮት ይቀራል፡፡ ይህ የድሮ ታሪክ አይደለም አሁንም ቢሆን በአንዳንድ የምዕራብ ባህል ገብቶናል ከሚሉ ጥቂት ከተሞቻቸዉ አልፎ አልፎ ከሚታዩ ጋብቻዎች ዉጭ አጠቃላይ የህንድ ማህበረሰብ ከሚመስለዉ ካስት ዉጭ ጋብቻ አይመሰርትም፡፡

    ይህ የማህበረሰብ ስደራ የሚሰጠዉ በሀብት፣ ባለዎት የበዛ ችሎታ (የአርስቶትል ማኅበረስብ እሳቤ መሰል Dominanat Appetite መሰረት ያደረገ) ፣ በሂደት በሚከዉኑት ሙያ አሊያም አኗኗር አይደለም ሲወለዱ የሚያገኙት እስኪሞቱ የማይለይ ኢሰብአዊ ድልድል ነዉ፡፡ በዚህ ስርአት ከላይ ያሉት ሶስቱ ከፍተኛ ካስት ሲሆኑ አራተኛዉ ሹድራ የሌሎቹ አገልጋይ ባሪያ ነዉ፡፡ ከዚህ የቫርና ስርአት ዉጭ ያሉት ሂነዱዎች እና አብዛኞቹ ሹድራዎች አይነኬ ተብለዉ ለሰዉ ልጅ የማይመጥን በደል ይደርስባቸዋል፡፡ የዚህ ፁሁፍ ርዕስ የሆነዉ ዶ/ር አምበድከር የሹድራ/አይነኬ አባል ነበር፡፡


    • ሐይማኖት እንደ መሣሪያ

    ይህ ቫርና በሂንዱ የሀይማኖት ስርዓት ድጋፍ ያለዉ ሲሆን ማንኛዉም ለካስቱ ከተመደበለት ስራ ዉጭ መስራት አይችልም ይህን ካደረገ ከሞት በሀኋላ የባሰ ግፍ እንደሚደርስበት በሐይማኖት እየተሰበከ ያድጋል፡፡ ለምን አኔ ሹድራ ሆንኩ ካለ በዛኛዉ ወደዚች አለም ከመምጣቱ አስቀድሞ የፈፀመዉ በደል እንደነበር ይነገረዋል፡፡ እናም በህንድ የሚኖሩ አይነኬዎች ለዘመናት (ከ2000 አመት በላይ) አገልጋይነታቸዉ እያስደሰታቸዉ ሌሎች ከላይ ያሉትን ሶስት ካስት ሲያገለግሉ ኖረዋል፡፡ ትምህርትንም አስመልክቶ ለካስቱ የተመደበዉን ኃላፊነት ለማከናወን ከሚጠቅመዉ ዉጭ መማር እንደማይቻል ይሰበካል፡፡ ለዚህም ነዉ የሹድራ አብዛኞቹ አባላት ያልተማሩ እና ያልነቁ የሆኑት፡፡ ለዚህ ‹ቫርና› ለሚሰኘው ስርዓት የሂንዱ ሐይማኖት ዋንኛ መነሻው ነዉ፡፡

    ይህ አፀያፊ እና ኢ-ሰብአዊ የህንድ ካስት ስርዓት የዱሮ ታሪክ ሆኖ አልቀረም፡፡ በቅርብ እንኳን በኔህሩ ዩኒቨርሲቲ በተደረገ ጥናት የካስት ስርአቱ በህንድ በአብዛኛዉ ገጠራማ አካባቢዎች መልኩን እየቀያየረም ቢሆን በመተግበር ላይ እንደሆነ ያመለክታል፡፡ ለዚህም ዋንኛዉ ምክንያት ስርዓቱ ከሂንዱ ሐይማኖት ጋር የተገናኘ እና በማኅበረሰቡ በሹድራ አባላት ጨምሮ ሰርፆ የገባ ስለሆነ በህግ በቀላሉ ለማስወገድ አለመቻሉ ነዉ፡፡

    የስርዓቱ መነሻ በግልፅ ካለመታወቁ ጋር ተያይዞ የተለያዩ እሳቤዎች የሚንፀባረቁ ሲሆን አንዳንዶች ከሂንዱ ሐይማኖት አመጣጥ ጋር ያያዙታል፡፡ እንደ ዶ/ር ቬሉ አንማሊ ገለፃ የህንድ ካስት ስርአት የመጣዉ በ1500 ኤ.ዲ አቅራቢያ ከሌላ አካባቢ (ከኢትዮጵያ እና ግብፅ) ከመጡ  ፀጉረ ልዉጥዎች ጋር በነበረ የረዥም ጊዜ ተደጋጋሚ ጦርነት በመጨረሻ አሸናፊ የነበሩት ቡድኖች ራሳቸዉን ብርሐማ (አምላክ እንደማለት ነዉ) ብለዉ በመሰየም እና ታላቅ ቦታ ለራሳቸዉ በመስጠት የተቀረዉን ማህበረሰብ ለመግዛት ይመቻቸዉ ዘንድ ሂንዱ የሚባል ሐይማኖታዊ መሳሪያ መስርተዉ አሁን ላለዉ ካስት ስርዓት ምስረታ እና ማኅበራዉ ዉድቀት ዳርገዉታል የሚል ነዉ፡፡ እናም ለዶ/ር ቬሉ ሂንዱይዝም እና  ብርሀሚኒዝም አንድ ናቸዉ የመጀመሪያዉ በሁለተኛዉ የተሰራ ነዉና፡፡ ሌላዉ አፈታሪክ አይነኬዎች ስጋ ተመጋቢ ስለሆኑ እና በወቅቱ የሞተ እንስሳ ስጋ ይበሉ ስለነበር በሽታ ይዘዉ ይመጣሉ ስለዚህ ከዚህ በሽታ ለመራቅ አትክልት ተመጋቢዎቹ አይነኬ አሏቸዉ የሚል ነዉ፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚያደርጉት አብዛኞቹ የከፍተኛ ካስት አባላት አትክልት ተመጋቢ መሆናቸዉን ነዉ፡፡ ይሁን እንጂ ሁሉም የላይኛዉ ካስት አባላት አትክልት ተመጋቢ ካለመሆናቸዉ ባሻገር ብዙ የሹድራ አባላት አትክልት ተመጋቢዎች ናቸዉ፡፡

    ---
    ይቀጥላል፡፡
    --- 
    ጸሐፊውን ለማግኘት bemanishe@gmail.com ላይ ይጻፉላቸው፡፡

    ልማት ሲሉ፥ ‘በኢትዮጵያ ልማት አለ‘ ማለታቸው ነው?


    በጣልያን የ5 ዓመት ወረራ ወቅት ኢትዮጵያ ከፍተኛ የመንገድ ግንባታን አስተናግዳለች፡፡ ከአዲስ አበባ በአራቱም አቅጣጫ ወደየክልሉ የሚፈሱት መንገዶች በጣልያን ነው የተቀየሱት፡፡ ሌላው ቀርቶ አሁን በቅርቡ በዘመነ ኢሕአዴግ የተገነባው እና ‹የሚሌኒየሙ ድልድይ› የተባለው ድልድይ አጠገብ ለብዙ ዐሥርት ዓመታት አገልግሎት የሰጠው ድልድይ የተገነባው በጣልያን ወረራ ጊዜ፣ በኢትዮጵያውያን ጉልበት እና በጣልያኖች ጥበብ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ኢትዮጵያውያን አባይን የሚሻገሩት ዐፄ ፋሲለደስ ባስገነቡት ድልድይ፣ አሊያም በዋና/በጀልባ ነበር፡፡

    ጣልያን እነዚያን መንገዶች ለምን ይገነባ እንደነበረ ለመረዳት ቢያንስ በዚህች አንቀጽ ስለቅኝ ግዛት ማውራት ያስፈልጋል፡፡ የአውሮጳ ቅኝ ገዢዎች አፍሪቃን መቀራመት ከመጀመራቸው በፊት አውሮጳቸውን በኢንዱስትሪ አጥለቅልቀዋት ነበር፡፡ ኢንዱስትሪዎቻቸውን ለመገንባት የሚፈጀውን የሰው ኃይል ለመሙላት አፍሪካ መጥተው ባሪያዎችን በወሰዱበት ወቅት ያዩትን ጥሬ ሀብት ለኢንዱስትሪዎቻቸው ለማቅረብ የሚያስችላቸውን ዘላቂ ስርዓት ለመዘርጋት ነው ወደአፍሪቃ ተመልሰው የመጡት፡፡ ስለዚህ በቅኝ ግዛት የሚይዟቸውን አገራት በመሠረታዊ ልማት ማሳደግ እና ሁሉንም ነገር በቁጥጥራቸው ስር ለማዋል ያለው ሚና ትልቅ ስለነበር ያለ የሌለ ኃይላቸውን በሙሉ እንደደረሱ በዚያ ላይ ያውሉ ነበር፤ ሌላው ቀርቶ በጦርነት ወቅት እንኳን ከፊት እየተዋጉ ከኋላ ይገነቡ ነበር፡፡ ምክንያቱም የመሠረተ ልማት ግንባታ ለዜጎች የሚሰጠው ፋይዳ አሌ የማይባል ቢሆንም ገዢው የሚፈልገውን እንዲፈፅምም ያስችለዋል፡፡

    ይህንን መጥቀስ ያስፈለገው በኢሕአዴግ ዘመን ያለውን ዓይነት ልማት የውጭ ወራሪዎችም ሳይቀሩ ያደርጉት የነበረ ዓይነት መሆኑን ለማስታወስ ሲባል ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ‹በመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ከዓለም ሦስተኛ ደረጃ ሲቀመጥ፣ አገሪቱን በግል ኢንቨስትመንት ግን ከመጨረሻ ስድስተኛ ደረጃ ላይ› እንዳስቀመጣት የዓለም ባንክ የሰሞኑ ሪፖርት ይነግረናል፡፡ የግል ኢንቨስትመንት በኢትዮጵያ ሙሉ ለሙሉ አልከሰመም እንዲባል ያደረገውም ቢሆን በጥቂት ባለሀብቶች እና በገዢው ፓርቲ አባላት፣ ደጋፊዎችና የስርዓቱ ተጠቃሚዎች የሚመሩ መካከለኛ አቅም ያላቸው ኢንዱስትሪዎች ኢንቨስትመንት ነው፡፡ ይህ ለአንድ ወገን መጠቀሚያነት ብቻ ሰለባ የሆነ የግል እና የመንግሥት ኢንቨስትመንት የኢትዮጵያ መንግሥትን የ‹‹ልማት እንቅስቃሴ›› ከቅኝ ገዢዎች የልማት እንቅስቃሴጋ እንድናመሳስለው ያስገድደናል፡፡

    ያም ሆኖ ግን ኢሕአዴግን ከወራሪው ፋሺስትጋ ማመሳሰል ጨካኝነትም፣ ኢ-ሚዛናዊነትም ሊሆን የሚችልባቸው ምክንያቶች አሉ፡፡ ሌላው ቢቀር ትንሽም የሚንቀሳቀሱት የግል ኢንቨስትመንቶች ንብረትነታቸው ያው ዜግነታቸው ኢትዮጵያዊ በሆኑ ሰዎች መሆኑ ከሚጠቀሱት አንዱ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት የሚያደርገውን መሠረታዊ ልማት ለአገሪቱ በሥጦታነት ያቀረበው ይመስል ስለሚመካበት እና ሥልጣኑን ለማስቀጠያነት የፕሮፓጋንዳ መሣሪያ ስላደረገው፣ ቅኝ ገዢዎች ሳይቀሩ የሚያደርጉት ነገር መሆኑን ለማስታወስ እና ሕገ መንግሥቱም ቢሆን በአንቀጽ 89 ላይ እንደሚደነግገው ኢትዮጵያውያን ሁሉ የምጣኔ ሀብት ዕድገቱ ተጠቃሚ የመሆን እና የተሻሻለ የኑሮ ሁኔታ እንዲያገኙ ፖሊሲ ከመቅረፅ እስከማስፈፀም ብሎም የሀብት ክፍፍል ፍትሐዊ እንዲሆን እስከማድረግ የሚደርስ ኃላፊነት ያለበት መሆኑን ማስታወስ የሚያስፈልግ ይመስለኛል፡፡

    ለመሆኑ ከፕሮፓጋንዳው በመለስ፣ የኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት የአንድ ታዳጊ አገር መሄድ ባለበት የምጣኔ ሀብታዊ ፍሰት እየፈሰሰ ነው ወይስ በዘፈቀደ የሚጓዝ? ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል የሚታይበት ነው ወይስ ጥቂቶች ሲበለፅጉ ብዙኃን የሚቆረቁዙበት? ተራ የበጀት ቁጥር ዕድገት ነው ወይስ በመጨረሻው ቀን የዜጎች ኑሮ አዎንታዊ ለውጥ የሚመዘገብበት?...

    የኢትዮጵያ ልማት፤
    ‹‹ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል››?

    በኢትዮጵያ የምጣኔ ሀብታዊ ዕድገት አለ፡፡ እንደምሳሌ (የከተሞቹን ‹ማስተር ፕላን› በሚገባ መጠበቃቸው፣ የመኪና ማቆሚያ ማስተረፋቸው፣ ለተፈጥሮ/አካባቢ ያላቸው ተስማሚነት /environment friendliness/፣ ለሕዝብ የሚበጅ አገልግሎት ሰጪነታቸው /ወይም ኪራይ ሰብሳቢ አለመሆናቸው/ ግን ቢሆንም፣…) በየከተሞቹ መሐል በየጊዜው የሚበቅሉ ሕንፃዎች በሽ ናቸው፤ (በታቀደላቸው ጊዜ የሚጠናቀቁት ከስንት አንድ መሆናቸው ባይወራም፣ በመዘግየታቸው የሚወጣባቸው አገራዊ ወጪ/ብክነት ባይነገርም፣ ከጥራታቸው ይልቅ ብዛታቸው ብቻ ቢደሰኮርም) የመሠረተ ልማት ግንባታዎች በርካታ ናቸው፤ (የዓመታዊ በጀቱ ሩብ ገደማ በለጋሽ አገራት የሚሞላ ቢሆንም፣ የዋጋ ግሽበቱ መቶኛ ከምጣኔ ሀብት ዕድገቱ መቶኛ ንፅፅር የሚበልጥ ቢሆንም) ሁለት አሐዝ ዓመታዊ የጠቅላላ ገቢ ዕድገት (GDP Growth) እየተመዘገበ ነው፡፡

    እነዚህን የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ተቃርኖዎች የዕድገት እና የልማት ልዩነት ውጤቶች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ‹‹ልማት›› እያለ የሚጠቅሰው ነገር እና የምናየው እንቅስቃሴ እውነትም አገሪቷ እየለማች ነው እንድንል ያስገድዱናል፡፡ በተቃራኒው የብዙኃኑ ኑሮ ከአምና ካቻምና እየከበደ እንጂ እየቀለለ አልሄድ ሲል እንደሚባለው ‹‹የልማቱ ወጪ›› ሊሆን ይችላል በሚል በእንቆቅልሽ እንኖራለን፡፡ በጅቡቲ ወደብ ‹‹ኢትዮጵያውያን የሚበሉት መኪና ነው ወይ?›› እስኪባል መኪና ወደአገር ውስጥ እያስገባን፣ ብዙ መኪና አለባት በምትባለው አዲስ አበባ 45 በመቶ የሚሆኑት ነዋሪዎች በአውቶቡስና ታክሲ የመጓጓዝ አቅም አጥሯቸው በእግር ነው የሚጓጓዙት ሲባል ሀብትና ዕድገቱ የት ሄደ ብለን ግራ እንጋባለን፡፡ በተለይ ‹ኢኮኖሚስት› ባለመሆናችን በኢኮኖሚ ሳይንስ ትክክለኛው ዕድገት ምትሀታዊ ለሚመስለን ሌሎች ባለሙያዎች ግራ እንደተጋባን አለን፡፡ እውን ግራ መጋባታችን የአለማወቃችን ውጤት ነው ወይስ የኢትዮጵያ የምጣኔ ሀብት ዕድገት ራሱ ነው ግራ ተጋብቶ ግራ የሚያጋባን?

    ዕድገት ወይስ ልማት (Growth Vs. Developtment)?

    በምጣኔ ሀብታዊ ኢኮኖሚክ ልማት ላይ ቀደምት ከሚባሉት ተመራማሪዎች መካከል አሜሪካዊው ፕሮፌሰር ማይክል ቶዴሮ ቀዳሚው ናቸው፡፡ ፕሮፌሰር ቶዴሮ ምጣኔ ሀብታዊ ልማትን ሲበይኑት ‹‹የኑሮ ደረጃ ማደግ፣ ሰዎች ለራሳቸው የሚኖራቸው ግምት መሻሻል ብሎም ከጭቆና ነጻ መውጣት እና በርካታ የሕይወት አማራጭ ማግኘት ነው›› ይላል፡፡

    በጀርመን አገር ነዋሪ የሆኑት ኢትዮጵያዊው የምጣኔ ሀብት ፕሮፌሰር ፈቃዱ በቀለ ‹‹እንደጂዲፒ የመሰሳሉት የዕድገት መለኪያዎች በቀጥታ የሒሳብ ስሌት (Linear Mathematic) ስለሚሰሉ የተወሳሰበውን የኢኮኖሚክስ ዓለምና ተለዋዋጩን የሰው ባሕርይና የፍጆታ አጠቃቀም አስልቶ ማቀረብ በፍፁም አይቻልም›› ብለው ጽፈዋል፡፡

    የምጣኔ ሀብት ዕድገት (Growth) የምጣኔ ሀብት ልማትን (Developtment) ያክል የሰፋ ጉዳይ አይደለም፡፡ ዕድገት የቁጥር ጉዳይ ሲሆን፣ ልማት ደግሞ የዜጎች ሕይወት ደረጃ መሻሻል ላይ ያተኩራል፡፡ ቢሆንም ግን የአንድ አገር ምጣኔ ሀብት ዕድገት ለልማት ከፍተኛ አስተዋፅዖ ስለሚያደርግ ወሳኝ ነው፡፡ በመሐከላቸው ያለው መሥመርም ቀጭን ነው… በተለይ ለለሙት አገራት (developed countries) የምጣኔ ሀብት ዕድገት የምጣኔ ሀብቱን ሁኔታ ለመለካት ይጠቅማል፡፡ እንደኢትዮጵያ ባሉ በመልማት ላይ ያሉ አገራት (developing countries) ግን ከዕድገት ይልቅ ልማት የዜጎችን የኑሮ ሁኔታ ከማሻሻል ረገድ በትክክለኛው የምጣኔ ሀብት መሥመር እንዲጓዙ ያግዛቸዋል፡፡

    ‹‹…የኢሕአዴግ መንግሥት በአለፉት ዐሥር ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በአማካይ ሲታይ 10 በመቶ እንዳደገ ሲነግረን ከርሟል። ይህንንም እነ ዓለም የገንዘብ ድርጀትና በጠቅላላው የዓለም የኢኮኖሚ ማኅበረሰባት ያረጋግጣሉ። ይሁንና ግን በኢኮኖሚ ዕድገት ታሪክ ውስጥ ስንትና ስንት የፈጠራ ሥራዎች በተካሄደባቸው የካፒታሊስት አገሮች ውስጥ እንደ ኢትዮጵያው ዓይነቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ታይቶ አይታወቅም። ለምሳሌ ፕሮፈሰር ሁንትና ፕሮፌሰር ሼርማን የሚባሉት ሁለት የአሜሪካ ፕሮፌሰሮች፣ Economy from a Traditional and Radical Point of View፣ በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ የአሜሪካን ኮንግረስ ያቀረበውን ሀተታ እንደዚህ ብለው ይመዘግባሉ። 1839-1879 . ባለው ጊዜ ውስጥ የአሜሪካን ኢኮኖሚ በግምት በተጨባጭ 4.3% 1879-1919 . ደግሞ 3.7% 1919-1959 . ባለው ጊዜ ውስጥ ደግሞ 3% እንዳደገ ይገልጻሉ። ለዚህ ዕድገት የአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ግኝት ወይም ፈጠራ 50% አስተዋፅዖ እንዳበረከተ ይናገራሉ›› በማለት ዶ/ር ፍቃዱ የዕድገቱ ቁጥር በራሱ አጠራጣሪ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ቁጥሩ በሚያከራክርበት ሁኔታ ‹‹አለ›› የሚባለው ዕድገት ልማትን ለማምጣት ይችላል ወይ የሚለው ጥያቄን ማሰቡ በራሱ ያስፈራል፡፡

    የኢንዱስትሪ እና የግብርና ዘርፍ ምርት እያሽቆለቆለ፣ የአገልግሎት (ሆቴል እና ቱሪዝም…) ዘርፉ ዕድገት ከታቀደው በላይ እየወጣ የ90 በመቶ አርሶ እና አርብቶ አደሮች አገሯ ዜጎች የኑሮ ደረጃ አድጓል ማለት አይቻልም፤ ዜጎች ከአገራቸው ለመውጣት የዱር አውሬ ሲበላቸውና የድንበር ጠባቂ ሲገድላቸው፣ የባሕር ሲሳይ ሲሆኑ እና በኮንቴነር ታፍነው ሲሞቱ ዜና በየዕለቱ እየሰሙ ዜጎች ለራሳቸው ያላቸው ግምት ጨምሯል ማለት አይቻልም፤ ዜጎች በ‹‹ፍርሐት ቆፈን›› በታሰሩበት እና ጭቆና በበዛበት ፖለቲካዊ ከባቢ እና የግል ኢንቨስትመንት በተዳፈነበት ገበያ አማራጮችን ማግኘት አይቻልም፡፡

    እንግዴህ - በዚህ ሁሉ ማግኘት ‹‹አይቻልም›› በሚል ቃል በተከበበት አገር ውስጥ ማይክል ቶዴል የሚበይንልን ‹ልማት› መፈለጋችንን ማቆም  አልያም የልማት ትርጓሜን  ደግመን መበየን ጊዜው አሁን ነው፡፡ ስለምን ልማትን ያለአገሩ ትፈልጉታላችሁ?
    ---
    *ጸሐፊው የኢኮኖሚክስ ባለሙያ ባለመሆኑ ሙያዊ ዕውቀት ያላቸው ድምዳሜውን እንዲሞግቱት በዚሁ አጋጣሚ ይጋብዛል፡፡

    Sunday, June 23, 2013

    ‹ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች›፡ የዴሞክራሲ ፀጋ ወይስ ፈተና?


    ዘላለም ክብረት

    ‹‹እኛ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች፡ በሀገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም፣ ዋስትና ያለው ዴሞክራሲ እንዲሰፍን…›› እያለ የሚጀምረው የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሕገ መንግስት፤ ዴሞክራሲን እና ሰላምን የማስፈን ሂደትን በዋናነት ‹ለብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች› በመስጠት፤ እንዲሁም ሉአላዊነትንም ‹ለብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች› በማጎናፀፍ፤ ኢትዮጵያ የምትወከለው በቡድኖች እንደሆኑ ያስረግጣል፡፡ [1]  እዚህ ላይ የሚነሳ ትልቅ ጥያቄ አለ፤ በሕገ መንግስቱ ‹ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች› በመባል የሚጠሩት የተለያዩ ዘውጎች ‹… ዴሞክራሲ እንዲሰፍን…› ማድረግ ይችላሉን? የሚል፡፡

    ዴሞክራሲ ምን ይፈልጋል?

    ዴሞክራሲ ሂደት እንጅ ግብ አይደለም ብለን ብንነሳም፤ የዴሞክራሲ የመጨረሻ ግቡ ግን የጋራ ሰላም (Mutual security) እና መልካም ሕይወት (Good life) እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ስለዚህም እነዚህን ዋነኛ ዓላማዎች ለማሳካት ዴሞክራሲ በዋናነት ከዜጎች እና ከፖለቲካው ተዋናዮች የሚፈልጋቸው ዋነኛ ግብአቶች አሉት፡፡

    የመጀመሪያው እና ዋነኛው የዴሞክራሲ ምሰሶ፤ ሰላማዊ እና ሕግን መሰረት ያደረገ ውድድር ነው፡፡ ይህም ማለት ዴሞክራሲ ዜጎች የሚሻላቸውን አካል የሚመርጡበት ስርዓት ነውና ተወዳዳሪዎች ሰላማዊ ይሆኑ ዘንድ ዴሞክራሲ ትፈልጋለች፤ ነውጠኛ አማራጭን ዜጎች የጋራ ሰላምን በዴሞክራሲ አማካኝነት ለመቀዳጀት የሚያደርጉትን ትግል እጅግ ይጎዳዋልና፡፡ ሌላው ከፖለቲካ ተዋናዮች የሚጠበቀው ቅድም ሁኔታ ደግሞ ሕግ አክባሪነት ነው፡፡ ምንም እንኳን የፖለቲካ ተዋንያን የተሻለ ሕግ እና ስርዓት ለዜጎች ለመስጠት ቢነሱም፤ የተሻለ ሕግ እና ስርዓት ለማምጣት ያለውን ሕጋዊ ስርዓት አክብረው ቢጀምሩ ለዴሞክራሲ መጠናከር ትልቅ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፤ አዲስ ስርዓትንም ‹ሀ› ብሎ ከመጀመር ይታደጋል፡፡

    እንግዲህ ሰላማዊነት እና ሕጋዊነት ከፖለቲካ ተዋንያን የሚጠበቁ ዴሞክራሲ ቅድመ ሁኔታዎች ከሆኑ፤ ከህዝቡስ ምን ይጠበቃል? የሚለው ጥያቄ ወሳኝነት ይከተላል፡፡ በህዝቡ ዘንድ በዋናነት እንዲዘጋጅ የሚጠበቀው የዴሞክራሲ ስንቅ ሰጥቶ መቀበል እና የጋራ ጥቅምን ማሰስ  (Cross cutting cleavage) ነው፡፡ ይሄም ማለት በሕዝቡ ዘንድ የዴሞክራሲ መዘርጋት ለሁላችንም የጋራ ሰላም ይሰጠናል፤ ስለዚህም ከራሴ/ከቡድኔ ጥቅም ይልቅ ይሄን ለሁላችንም ጥቅም ሊሰጠን የሚችልን አካሄድ መምረጥ አለብኝ ብሎ ማሰብ ነው፡፡ የጋራ ጥቅምን ከማስፋት ይልቅ መግፋትን በሚመርጥ ሕብረተሰብ ውስጥ ዴሞክራሲን መመስረት የማይቻል እንደሆነ ዘርፍ አጥኝዎች የብዙ ሀገራትን ተሞክሮ በመውሰድ የሚያሳዩት ጉዳይ ነው፤ ምክንያቱም የዴሞክራሲ ዋነኛ ግብ የጋራ ሰላም (Mutual security) እና መልካም ሕይወት ነውና፡፡

    የዘውግ ባህሪያት ለዴሞክራሲ

    ዴሞክራሲ የጋራ ሰላም ማምጣትን እንደ ግብ ከያዘ፤ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ በዘውግ (Ethnically divided) በተካፋፈሉ ሀገራት ምን መልክ ይኖረዋል? የሚለው ጥያቄ ምላሽ የሚሻው የርዕሰ ጉዳያችን አበይት አጀንዳ ነው፡፡ ዴሞክራሲ ምን እንደሚፈልግ ከላይ ለመግልፅ እንደሞከርነው ሁሉ ዘውግ (Ethnicity) የራሱን ፍላጎቶች እና ዓላማ እንዳለው ማሳየትም ጉዳዩን የበለጠ ግልፅ ያደርገዋል፡፡

    Donald Horowitz ‘Ethnic Groups in Conflict’ ባሉት ስራቸው የዘውግ ግንኙነትን ሲገልፁ ‹Ethnic affiliations are Powerful, Permeative, Passionate and Pervasive› በማለት ነው፡፡ ይህም የሚነግረን እውነት፤ ሰዎች የዘውግ ግንኙነታቸው የነሱን ሁሉንም ነገር እንደሚወስን እና በቀን ተቀን ሕይወታቸው ውስጥ ሁነኛ ቦታ ያለው የባህሪ ወሳኝ አድርገው እንደሚወስዱት ነው፡፡

    Thursday, June 20, 2013

    ‹በሲቪል ሶሳይቲ ያደገ ሀገር የለም!› የኢትዮጵያ መንግስት፤ ‹ያለ ሲቪል ሶሳይቲ ድጋፍ የተመሰረተ ዲሞክራሲስ አለን?› እንጠይቅ




    ሲቪል ሶሳይቲው ከየት መጣ ያልተባለ ካቴና እጁን ጠፍሮ ሊያስር ወደሱ እየመጣ መሆኑን ተመልክቶ፤ ለመንግስትን ‹እባክህ ካቴናው እጄ ላይ ከመታሰሩ በፊት እንወያይ› የሚል ልመና አቀረበ፡፡ መንግስት ግን ‹እዚህ የተቀመጥኩት ሕብረተሰቡን ከጥፋት ለመከላከል ነው› በሚል ምክንያት ለልመናው እቁብ ሳይሰጥ ካቴናውን ይዞ ወደ ፓርላማ አቀና፤ ፓርላማውም በአብላጫ ድምጽ ሲቪል ሶሳቲው ይታሰር ዘንድ ወሰነ፡፡ ዴሞክራሲያችን እና ፖለቲካችን ‹የተለየ ተልእኮ› ይዘው ሲዘውሩ ከነበሩት ‹የህዝብ ጠላቶች› መካከልም፤ እስሩን የቻሉት ተስፋን ሰንቀው በእስር ላይ ይገኛሉ፤ ያልቻሉት ደግሞ ወደ ሞት አቅንተዋል፡፡ ይህ እንግዲህ ያለፉት 5 ዓመታት የኢትዮጵያ ሲቪል ሶሳይቲ አጭር የሕይወት ታሪክ ነው፡፡

    ቶኮክቪል በአሜሪካ፤ ፑትንሃም በጣሊያን

    የ19ኛው ክፍለ ዘመኗን አሜሪካ የወንጀል ስርዓት ለማጥናት ከጓደኛው Gustave Bonninière ጋር በመሆን በአሜሪካ ምድር የተገኝው Alexis de Tocqueville የተልዕኮው ምክንያት የሆነውን የአሜሪካ የወንጀል ስርዓት ለፈረንሳይ እንዴት ሊጠቅም እንደሚችል በሪፖርት መልክ አቀረበ፡፡ ነገር ግን ሪፖርቱ የታሰበውን ያክል አዲስ ነገርን የያዘ አልነበረም፡፡ ይልቁንም ቶኮክቪል ወደ ፈረንሳይ ከተመለሰ በኋላ በሁለት ጥራዝ የፃፈው ‘Democracy in America’ የተባለው ስራው ዘመን ተሸጋሪ ሆኖ እስከ አሁን ድረስ ተጠቃሽ ሆኖ እናገኝዋለን፡፡ በዚህ ታላቅ ስራው ቶኮክቪል ስለ አሜሪካ የህግ አውጭ አካል፤ ስለ የፖለቲካ ተቋማት፤ ስለ ፕሬሱ ወ.ዘ.ተ ሰፊ ትንታኔን አቅርቧል፡፡ ለአሜሪካ ዴሞክራሲ መጠናከር ዋነኛ አስተዋፅኦ ያደረጉት ተቋማት የሲቪል ሶሳይቲው እና የተለያዩ የዜጎች ማህበራት (Citizens associations) ናቸው፤ በማለትም የነዚህን ተቋማት ወሳኝነት ሲያስረዳ ‹ማህበራት ሁሉም የህብረተሰቡ አካል ስለ ህብረት የሚማርባቸው እንደ ትልቅ ነፃ ትምህርት ቤት ናቸው፡፡›› በማለት ነው፡፡ ሲቀጥልም “[…] the voluntary association of the citizens might supply the individual exertions of the nobles, and the community would be alike protected from anarchy and from oppression.” እያለ እነዚህ ማህበራት ዜጎች ራሳቸውን ከጭቆና ይከላከሉባቸው ዘንድ የሚጠቅሙ የመብት ጋሻዋች እንደሆኑ ይገልፃል፡፡

    ሮበርት ፑትንሃም በበኩሉ ‘Making Democracy Work’ ባለው የጣሊያንን ሕብረተሰብ የዴሞክራሲ መስተጋብር ባጠናበት ስራው፤ ዜጎች በብዛት እና በንቃት በሲቪል ማህበራት ውስጥ ሲሳተፉ፤ የመንግስት ተቋማት ላይ ያላቸው ክትትል (Watchdog role) ይጨምራል፤ በዚህም ምክንያት የመንግስት ተቋማት ውጤታማነት ከፍ ይላል› የሚል መደምደሚያ ላይ ያደርሰናል፡፡

    ‹የዴሞክራሲው ማዕከል ዜጎች ናቸው› ከሚለው እሳቤ በመነሳት አብዛኞቹ የዘርፉ ምሁራን በዴሞክራሲ ውስጥ የዜጎች ተሳትፎ ወሳኝ እና ተተኪ የሌለው አካሄድ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ዜጎች የዚህ ተሳትፎ ዋነኛ ተዋናይ ይሆኑ ዘንድ ደግሞ ዜጎች ከመንግስት ተግባራት ጎን ለጎን የራሳቸውን ክትትል እና አስተዋፅኦ የሚያደርጉበት መንገድ ከመንግስት ነፃ የሆነ፤ በዜጎች ነፃ ፈቃድ የተመሰረተ፤ ራሱን በራሱ ያደራጀ እና ለሕግ ተገዥ የሆነ አካል ያስፈልጋል - ሲቪል ሶሳይቲ፡፡


    ዴሞክራሲ ያለሲቪል ሶሳይቲ

    ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የዴሞክራሲ መነሻው እና መድረሻው ዜጎች ናቸው፡፡ ዜጎች ወግና ስርዓት ያስጠብቅ ዘንድ የሚሾሙት፤ ሲፈልጉም በምትኩ ሌላ የሚተኩበት የዜጎች ‹ሎሌ› የሆነ አካል ደግሞ መንግስት ነው፡፡ እንግዲህ በዴሞክራሲያዊ ስርዓት የመንግስት እና የዜጎች ግንኙነት የጌታ እና ሎሌ ነው ማለት ነው፤ ዜጎች ጌታ፣ መንግስት ሎሌ፡፡ ጌታ ለሎሌው ትእዛዝ እንደሚሰጥ ዜጎችም ለመንግስት በህግ የተደነገገ መብት እና ግዴታ ሰጥተው መንግስት ምህዋሩን ስቶ ያለስልጣኑ በዜጎች ሕይወት ላይ ጣልቃ እንዳይገባ ደግሞ በተለያዩ መንገዶች ክትትል ያደርጉበታል፡፡ ሲቪል ሶሳይቲው እንግዲህ በዜጎች ተመስርቶ መንግስት ሊያከናውናቸው የማይችላቸውን ተግባራት ያከናውናል እንዲሁም መንግስት አጉራ ዘለል ሲሆን ‹ተው ተመለስ› እያለ የጥበቃ ስራን ይሰራል፡፡ በዚህም ምክንያት በዴሞክራሲያዊ ማህበረሰብ አወቃቀር ውስጥ ሲቪል ሶሳይቲው ሰፊና ሁነኛ ድርሻን ይይዛል፡፡

    ከዚህ በታች በሚታየው የሶስት የስርዓት አይነቶች ንፅፅር የሲቪል ሶሳይቲውን ድርሻ እንመልከት፡፡


    ከንፅፅሩ እንደምንረዳው በዴሞክራሲያዊ ስርዓት (Democratic System) ውስጥ መንግስት ቁጥብ ድርሻ ያለው ሲሆን፤ ሲቪል ሶሳይቲው ደግሞ በመንግስት እና በሰፊው ሕዝብ (Parochial Society) መካከል ተሰይሞ የተሳትፎ ድልድይ በመሆን ያገለግላል፡፡ በአምባገነን ስርዓት (Authoritarian System) ደግሞ የመንግስት (Party State) ድርሻ ከፍ በማድረግና የራሱን የሙያ ማህበራት (State controlled associations) በመመስረት ሲቪል ሶሳይቲውን የማያላውስ ጠባብ መንገድ ላይ ያስቀምጠዋል፤ ሲብስም ሲቪል ሶሳይቲው በህቡዕ እንዲንቀሳቀስ ያስገድደዋል፡፡ በፈላጭ ቆራጭ ስርዓት (Totalitarian System) ደግሞ ከናካቴው ሲቪል ሶሳይቲ የሚባለውን ሀሳብ አናገኝውም፡፡


    እንግዲህ ዴሞክራሲ የሕዝብ ልህዝብ በሕዝብ ቆመ ስርዓትነቱ የዜጎችን ተሳትፎ ወሳኝ ያደርገዋል፡፡ ያለዜጎች ተሳትፎ ዴሞክራሲ ሊኖር አይችልም ወደ ሚለው ድምዳሜ ያመራናል፡፡ የዜጎች ተሳትፎ ዋነኛ መሳሪያ የሆነው ሲቪል ሶሳይቲ ደግሞ ይህን የዜጎች ተሳትፎ እውን ያደርጋል እና ዴሞክራሲን ያለ ሲቪል ሶሳይቲው ማሰብ ቅዥት ይሆንብናል፡፡


    The Ethiopian ‘War’ on the Civil Society


    ‹ቡርኪናፋሶ ስልሳ ሽህ ሲቪል ሶሳይቲ አለ፤ ነገር ግን ስድስት ሽህ የሚሞሉ የንግድ ድርጅቶች ግን የሉም፡፡ ደቡብ ሱዳን ገና ሪፈረንደም እንኳን ሳታካሂድ ከሁለት ሽህ በላይ ሲቪል ሶሳይቲ ፈልቶባታል፤ ነገር ግን በቅጡ 200 እንኳን የሚሞሉ የንግድ ድርጅቶች እንኳን የሏትም፡፡›› የሚለው ሀሳብ ከመንግስት ሰፈር ምርጫ 97ን ተከትለው ሲሰሙ ከነበሩ ድምፆች ዋነኛው ነው፡፡ ታዲያ ይሄ ምን ችግር አለው? ብሎ መጠየቁ እዚህ ላይ ተገቢ ይሆናል፡፡ የሲቪል ሶሳይቲው መብዛት በራሱ ጥፋት ሊሆን አይችልም፤ ይልቁንም ለሕግ ተገዥነታቸው እና ነፃነታቸውን አስጠብቀዋል ወይስ ተላልፈዋል? ነው መጠየቅ ያለበት ተገቢ ጥያቄ፡፡ መንግስት ከሲቪል ሶሳይቲው ጀርባ በመሆን የሲቪል ሶሳይቲውን የገንዘብ ምንጭ በማድረቅ ከማጅራቱ ላይ መትቶ ሲጥለው፤ ‹ይህ ገደብ በመብት ዙሪያ የሚሰሩ ድርጅቶችን ብቻ ነው የሚመለከተው› ማለቱ ደግሞ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል፤ ምክንያቱም ሲቪል ሶሳይቲው በዋናነት የሚፈለግበት መስክ የመብት ጉዳይን በሚመለከቱ ወረዳዎች ነውና - የሰፊው ሕዝብ እና የመንግስት አገናኝ ድልድይ በመሆን፡፡ በተጨማሪም ምንም እንኳን መንግስት ‹ዴሞክራሲ ወይም ሞት› በሚለው አደባባይ መሃላው የምናውቀው ቢሆንም፤ የንግድ ድርጅቶችን መበርከት ታሳቢ አድርጎ ‹በሲቪል ሶሳይቲ ያደገ ሀገር የለም› ሲል፤ ‹ልማትን ጠበቅ - ዴሞክራሲን ለቀቅ› አድርጎ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነም ያስረዳናል፡፡


    መንግስት በዚህ አላቆመም፤ ሲቀጥል ‹ዴሞክራሲን በጡጦ አንጠባም›፣ ‹ዴሞክራሲ ከዋሽንግተን ወይም ከብራሰልስ የምንገዛው ሸቀጥ አይደለም›፣ ‹የትሮይ ፈረስ ከቅጥሩ አልፎ ወደ ትሮይ ይገባ ዘንድ አንፈቅድም፤ በውስጡ ወታደሮች እንዳሉ እናውቃለንና› ወ.ዘ.ተ የሚሉ መከላከያዎች ሲቪል ሶሳይቲውን ሲከስ የሚያነሳቸው ልምጮች ናቸው፡፡ ለዚህም ዋነኛ ምክንያቱን ሲያስቀምጥ ዴሞክራሲና የፖለቲካ ተሳትፎ ለዜጎች እና ለዜጎች ብቻ የሚተው ነው የሚል ነው፡፡ ከምዕራቡ ዓለም የሚመጣው ገንዘብ የዜጎችን መብት ቀምቶ በነሱ ፋንታ ሊያዝ፤ ሊወስን አይችልም የሚል ነው፡፡ ይሄን ሀሳብ ለማፅናትም ሉዓላዊነትን እንደ መከታ ያነሳል፡፡ በርግጥ በዘመናዊው እሳቤ ሉዓላዊነት ጥፋትን መመከቻ ሆኖ የሚቀርብ ጋሻ አይደለም፤ ይልቁንም ዜጎችን ባለመበደል እና የዜጎችን ሉዓላዊነት በማክበር፤ መንግስት የዜጎች ተወካይ ሆኖ በዓለማቀፍ መድረክ የሚታይበት ልብስ እንጅ፡፡ በሉዓላዊነት ሰበብ የተከለከለው ገንዘብ፤ በመብት ዙሪያ የሚሰሩ የራሱ የመንግስት ተቋማት ከምዕራብም ከምስራቅም እንደሚቀበሉና፤ ጥቅም ላይ እያዋሉት እንዳለ ስናይ ደግሞ ነገሩ የበለጠ ብዥታን ይፈጥርብናል፡፡


    ‘ፃዲቁ’ ሲቪል ሶሳይቲ


    ከላይ በመግቢያችን እንደጠቀስነው ከሲቪል ሶሳይቲው ዋነኛ ባህሪያት አንዱ ሕግ አክባሪነት ነው፡፡ ሲቪል ሶሳይቲው ህጋዊ ስርዓቱን ሕግን በመጣስ ለመገዳደር የሚሞክር ከሆነ ያኔ ሲቪል ሶሳይቲው ‹ሲቪል› የሚለውን ስሙን ያጣል፤ ጎራውንም ይለውጣል፡፡ ይህ ለሕግ ተገዥ ያለመሆንም ነው አንዳንድ ሲቪል ሶሳይቲዎችን ወደ ‘Uncivil Societyነት’ የሚመራቸው፡፡ ከዚህም በመለስ ሲቪል ሶሳይቲው በሕግ እና በስርዓት ካልተመራ ራሱን እንደህዝቡ አዳኝ በመቁጠር እና የተቃውሞ ባህልን (Oppositional Culture) በማዳበር የገለልተኝነት ባህሪውን ሊያጣ ይችላል፤ መንግስት ሊመልሰው ከሚችለው በላይ የበዙ ጥያቄዎችን በማቅረብ በተግባር ደረጃ እውን የማይሆኑ ህልሞች ላይ ጊዜውን ሊያጠፋ ይችላል፤ በተጨማሪም በአንድ ሀገር ውስጥ መረን የለቀቁ ብዙ የሲቪል ሶሳይቲ ባለ ቁጥር የፍላጎት እና የአካሄድ አለመጣጣም እንዲኖር በማድረግ ወደ ማህበራዊ ተቀርኖ እና ጽንፍ የያዘ የፖለቲካ ምህዳርን ወደ መፍጠር በማዘንበል ጉዳት ሊያስከትሉ ይችላሉ፡፡


    እነዚህን የሲቪል ሶሳይቲው ‹ሀጥያቶች› ለመከላከል እና ለማረም በሚልም የሕግ ማእቀፍ ሊወጣ ይችላል፡፡ ነገር ግን ሕጉ ሃጣንን ከፃድቃን ያልለየ ሲሆን ሲቪል ሶሳይቲው በአጠቃላይ ሊጫዎት የሚችለውን ዴሞክራሲን የመደገፍ ሚና ያጣል፤ ከዚህም ኪሳራ ዋናኛው ተጎጂ ሰፊው ሕዝብ ይሆናል ማለት ነው፡፡


    የኢትዮጵያ መንግስት ሲቪል ሶሳይቲውን በህግ ጥላ ስር አውላለሁ በማለት የህግ ማዕቀፍ መዘርጋቱ መልካም ቢሆንም፤ የህግ ማዕቀፉ ‹እኔን የሚተችን ሁሉ አያሳየኝ› በሚል መነሻ ሲሆን ግን ጉዳቱ ለሁሉም ይሆናል፡፡ ሲቪል ሶሳይቲውን ‹ጭጭ› አደረኩት የሚለው የመንግስት ፉከራ፤ ‹እሰይ ቤቴ በመቃጠሉ፤ ከቁንጫው ተገላገልኩ› ከሚለው ‘ደስተኛ’ ሰው የሚለይ አይሆንም፡፡ ቤቱ ቁንጫ ሊያፈራ ይችላል፤ መፍትሄውም ቤትን ማጽዳት እንጅ ፤ ቤትን አቃጥሎ ቁንጫውም ከቤቱ ጋር አብሮ ስለተቃጠለ መደሰቱ፤ ዘላቂ አይሆንም፡፡ ይልቁንም ሲቪል ሶሳይቲው መንግስትና ሕዝብን የሚያገናኝ ድልድይ ነውና፤ ድልድዩን መጠገን እና ማስተዳደር መልካም ሲሆን ማፍረሱ ግን ከሕዝብ ጋር መቆራረጥ፤ ዴሞክራሲንም ከበር እንደመመለስ ይሆናል፡፡