Saturday, February 23, 2013

የቅድመ ምርመራ ቅድመ ምርመራ





ስለ ቅድመ ምርመራ ስናወራ ሃሳቡን በጠንካራ ሁኔታ ተግባራዊ ያደረገው የደርግ መንግስት ሳይጠቀስ አያልፍም፡፡ ከዚያ በፌት በነበረው ጊዜ ‹ንጉሥ አይከሰስ ሰማይ አይታረስ› የሚለው አስተሳሰብ በስፋት ስለሚታመንበት ንጉሡን ከሚያወድስ እና የንጉሡን ፈቃድ ከሚያሟላ የህትመት እና የብሮድካስት  ስራዎች ውጪ ለመስራት ሃሳብ አልነበረም፡፡ የደርግ መንግስት የንጉሡን ስርዓት ካስወገደ በኋላ ደግሞ የቅድመ ሳንሱር ጉዳይን ጠበቅ ባለ በሕግ ደንግጎ ቀረበ፡፡ ሳንሱር ሳይደረጉ መፅሃፍት አይታተሙም፡፡ ሌሎች የህትመት ውጤቶችም የሚያስተላልፉት መልዕክት ስርዓቱ የሚደግፈውን ርዕዮተ ዓለም ፅንሰ ሃሳብና አስተሳሰብ ብቻ ነበር፡፡ በሃገራችን ባይታተምም ውጭ ሃገር የታተሙ ከስርዓቱ ጋር የሚፃረር ወይም የሚተች መልእክት ያለውን መፅሃፍ/የህትመት ውጤት ለማንበብ እንኳን አይቻልም፤ ወይም እንደ ሰረቀ ሰው ተደብቀው ነበር የሚያነቡት፡፡

ከደርግ ቀጥሎ የመጣው የኢህአዴግ መንግስት ደግሞ የህትመት ነፃነት ያስፈልጋል በሚል ቅድመ ምርመራም ክልክል እንደሆነ አወጀ፡፡

አንቀፅ 29.3 ሀ/ ‹‹የቅድሚያ ምርመራ በማንኛውም መልኩ የተከለከለ መሆኑን››

ይህን ህግ መሰረት በማድረግም በሬድዬና ቴሌቭዥን ደረጃ የታየ ለውጥ ባይኖርም ብዙ የግል ሃሳብ የሚንፀባረቅባቸው ጋዜጦችና መፅሄቶች ተፈለፈሉ፡፡ ለ97 ሃገራዊ ምርጫም እነዚህ የግል የህትመት ውጤቶች ህብረተሰቡን በማንቃት እና የሃራቸው ፖለቲካ ጉዳይ ያገባኛል ብለው እንዲያስቡ በማድረግ ረገድ አሉታዊ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ኢህአዴግም በምርጫው ውጤት እና በህዝቡን ስሜት ተደናግጦ ይመስላል ከ97 ምርጫ በኋላ በሰበብ አስባቡ ጋዜጠኖችንና አዘጋጆችን ማሰር እንዲሁም ለራሱ የሚመች ለትርጉም የማይመች እና ከፕሬስ ጋር የተያያዙ ህጎችን ማውጣት እና ተግባራዊ ማድረግ የጀመረው፡፡

Friday, February 22, 2013

#Ethiopia, #StopCensorship: ሳንሱር ዋጋ ያስከፍላል


በናትናኤል ፈለቀ

ለምዕራባዊያኑ የመጨረሻ  ወር በሆነው ዲሴምበር ወር መጀመርያ በሀገረ አሜሪካ ኢትዮጵያዊውን ጦማሪ እና እስክንድርነጋን ለማሰብ የተዘጋጀ መድረክ ነበር፡፡ በመድረኩ ላይ ስለ እስክንድር ነጋ የተናገሩት ተዋናይ ሊዬቭ ሽሬ የይበር እና ጸሐፊ ካርል በርንስቴይን ነበሩ፡፡ በርንስቴይን  ከ40 ዓመታት በፊት የዋሽንግተን ፖስት ዘጋቢ ሆኖ በሚሠራት ወቅት ከባልደረባው ቦብ ዉድወርድ ጋር በመሆ ን በአሜሪካ መንግስት ታሪክ ትልቅ የተባለውን እና የዋተርገቱ ቅሌት በመባል ሚታወቀውን የመንግሥት ባለሥልጣናት ያሳተፈ የሙስና ቅሌት አጋልጠዋል፡፡ በነዚህ ሁለት ዘጋቢዎች ታሪካዊ ማጋለጥ ምክንያት በወቅቱ አሜሪካን በፕሬዝዳንትነት ይመሩ የነበሩት ሪቻርድ ኒክሰን ስልጣናቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንዲለቁ ሆኗል፡፡

የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሳሌ ተደርጋ የምተጠቀሰው አሜሪካ በወቅቱ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ አቅም የሚያንሳት ሀገር አልነበረችም፡፡ የፖለቲካ ባህሏም  (በጥቅሉ) ተጠያቂነትን የሚያበረታታ እና ሙስናን የመሰሉ ተግባራትን አፀያፊ አድርጎ የሚቆጥር ነበር/ነው ማለት ይቻላል፡፡ በዚህም ሥርዓት መሐከል ግን እንክርዳድ አይጠፋውም፡፡ እናም መደበኛው የተጠያቂነት ሥርዓት ያልደረሰበትን ማማ አራተኛው የመንግሥት ክንፍ  (fourth organ of government) በመባል የሚታወቀው ሚዲያ አጋለጠው፡፡

ነጻ የሆኑ መገናኛ ብዙኃን መኖር እና ዜጎች ሐሳባቸውን መግለጽ እና መወያየት መቻላቸው የመንግሥትን እና የባለሥልጣናቱን ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ እንዲሁም ሕዝብን ከአደጋ ለመጠበቅ ቁልፍ መሣሪያዎች ናቸው፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ደሃ ሀገራት እያንዳንዱ የመንግሥት መዋለ ነዋይ ለሚፈለግለት ዓላማ መዋል አጥብቆ የሚፈለግ ነገር ነው፡፡ እውነታው ግን ይሄ አይደለም፡፡ በደሃ ሀገራት ስልጣን የሚይዙት ሰዎች/የፖለቲካ ፓርቲዎች ግን አንድም የራሳቸውን ግለሰባዊ ችግር ከሀገሪቱ ችግር በማስቀደም ወይንም በስግብግብነት አልፎ አልፎም ደግሞ ከብቃት ማነስ ሀገራቸው እጅግ አድርጋ የምትፈልገውን መዋለ ነዋይ ያባክናሉ፡፡ ይባስ ብሎም አብዛኞቹ ደሃ ሀገራት የሚመሩት ሁሉንም ነገር መቆጣጠር በሚፈልጉ እና ለምንም አይነት ነጻነት እና መብት ደንታ በማይሰጣቸው መሪዎች  (totalitarian) ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የሀገር ሃብት ሲመዘበር እና አለአግባብ ጥቅም ላይ ሲውል ለምን ብሎ የሚጠይቅ አካል አይኖርም፡፡ ካለምፍዳው እጅግ ብዙ ይሆናል፡፡

Thursday, February 21, 2013

ሳንሱር እና ሕግ፡ ከትናንት እስከዛሬ



የሰው ልጅ ሐሳቡን ለሌላው መግለጽ መጀመሩ ሰዎች የጋራ ባሕርያትን ይዘው ወደ አዲስ ስልጣኔ፤ ወደ አዲስ ሕይወት እንዲወጣ አድርጎታል፡፡ ነገር ግን የዚህ ትስስር ድንበር የለሽ መሆን ጉዳት አለው በማለት፤ በተለያዩ ወቅቶች በተለያዩ ምክንያቶች መረጃን የመለዋወጡ ሂደት ገደብ እንዲኖረው ይደረጋል፡፡ ገደብ እንዲደረግ የሚያስገድዱት ዋነኛ ምክንያቶች ሦስቱን ዋነኛ ተቋማት መጠበቅ በሚል ሐሳብ ስር ይጠቃለል፡፡

እነዚህም ተቋማት ቤተሰብ፣ ቤተ እምነት እና ቤተ መንግሥት ናቸው፡፡ ቤተሰብን መጠበቅ ስንል ቤተሰብ የኅብረተሰብ መሠረት በመሆኑ ቤተሰብን እና ስርዓቱን የሚጎዱ ነገሮች (Obscene) በአደባባይ እንዳይኖሩ ማድረግ ማለታችን ነው፡፡ ቤተ እምነትን የሚያጎድፉ ነገሮችም (Blasphemous) እንዲሁ:: እንዲሁም በሦስተኝነት በሕግ የተዘረጋውን ስርዓት ለመጠበቅ ሲባል ሲሆን  ይሄም የግደባ ሂደት ሳንሱር (Censorship) ይባላል፡፡

የሕግ ማዕቀፉ እና ልምዱ ምን ይላል?
 
ከላይ የጠቀስናቸውን ሦስት ተቋማት ከመጠበቅ አንፃር የተለያዩ ሀገሮች የተለያየ የህግ ማዕቀፍ ዘርግተው ጥበቃ ያደርጋሉ፡፡ ከጥንታዊቷ ሮም እስከ የዘመናችን ነጻ እና ለዘብተኛ (Liberal) ሀገሮች ድረስ በተለያዩ ምክንያቶች በመነሳት የሐሳብ ዝውውርን በሕግ ሲገድቡ ነበር፤ አሁንም ይገድባሉ፡፡ ነገር ግን የሕግ ገደቡ ያለ አግባብ ተለጥጦ የግለሰቦችን መብት መግፈፍ ሲጀምር ያኔ የገደቡ ስህተት ይጀምራል፡፡ ለምሳሌ የሮማን ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ከመካከለኛው ዘመን መጀመሪያ ጀምሮ ለተከታዮቹ 500 ዓመታት፤ አብዛኛውን የሳይንስት አስተምህሮቶች (የጋሊሊዮን መሬት በፀሐይ ዙሪያ ትሽከረከራለችን የሚል እሳቤን ጨምሮ) እንደ የኑፋቄ ትምህርት (Heresy) በመቁጠር፤ በኅብረተሰቡ ውስጥ ምንም ዓይነት ስርጭት እንዳይደረግ በማለት በሕግ ገድባ ቆይታለች፤ ሕጉንም የተላለፉትን ከእስራት እስከሞት ትቀጣ ነበር፡፡ ይሄም የተደረገው የሕግ ገደብ የሳይንሱን ዕድገት አቀጭጮት ነበር፡፡ በጥቅሉ አሁን ባለው አለም አቀፍ እሳቤ ሕሳብን ማሰራጨት ሙሉ ለሙሉ የተፈቀደ መብት (Absolute Right) እንዳልሆነ ጥቅል ስምምነት ቢኖርም፤ ገደቡ ከየት ይጀምር የሚለው ግን አከራካሪ ነው፡፡

ምኑ ይገደብ?

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ሊገደብ የሚገባው መብት የትኛው መሆን አለበት የሚለው ሐሳብ ስምምነት  ላይ ያልተደረሰበት ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን እንደ ኀልዮት ሊቃውንት የተለያየ ሐሳብ ይሰነዝራሉ፡፡ መንግሥት ራሱን እንደ ጠባቂ እና ሁሉን አድራጊ (state as Big Brother) በማድረግ ይህ የተፈቀደ ነው፤ ይህ ደግሞ የተከለከለ ነው የሚል ከሆነ የዜጎችን መብት ሊያቀጭጭ ይችላል የሚለው እሳቤ አንዱ ነው፡፡ ይህም - ይሄን ብትናገር፣ ብትጽፍ፣ ብታሰራጭ ዋ! - ማለት ሳንሱር በማስፈራራት (Censorship through intimidation) የሚለው ሐሳብ ነው፡፡ ሊቃውንቱም ይህ መሆን የሌለበት ነገር ነው ይላሉ፡፡

Wednesday, February 20, 2013

ግልጽ ደብዳቤ ለአቶ ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል እና ለአቶ በረከት ስምኦን


ለተከበሩ አቶ ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል፤ የኮሙኒኬሽን እና ኢንፎርሜሽን ሚኒስቴር ሚኒስትር፣
ለተከበሩ አቶ በረከት ስምኦን፤ በሚኒስትር ማዕረግ፣ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ፣

ከ20 ዓመታት በፊት ፓርቲዎቻችሁ - ሕወሓትም ሆነ ብአዴን - ብዙ የኢትዮጵያ ልጆች ሕይወታቸውን የገበሩለትን ጦርነት ያካሔዱት፥ ኢትዮጵያውያን ‹‹ጀርባቸውን ሳይመለከቱ›› በነጻነት አመለካከታቸውን እና ሐሳባቸውን እንዲያንፀባርቁ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ይህ ብዙዎች ደማቸውን ያፈሰሱለት፣ በሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ የተሰየመለት (አንቀጽ 29) ‹‹የአመለካከት እና ሐሳብን በነጻ የመያዝና የመግለጽ መብት›› ከኢትዮጵያውያን እጅ ቀስ በቀስ አፈትልኮ እየወጣ መሆኑ ቢያሳስበኝ ይህንን ግልጽ ደብዳቤ ለመጻፍ ተገደድኩ፡፡

ደብዳቤዬን መስመር ለማስያዝ እንዲመቸኝ ከኔ የተሻለ የምትረዱትን ነገር በማስታወስ ልጀምር፡፡ ኢትዮጵያ ከ80 ሚሊዮን የሚልቁ ሕዝቦች፣ ከ80 የሚልቁ ብሔሮች እና ብሔረሰቦች፣ በርካታ ሃይማኖቶች፣ እምነቶች እና ባሕሎች ያሏት አገር ናት፡፡ ሁሉም የየራሱ የሆነ ነገሮችን የሚረዳበት መንገድ ያለው ይህ ብዝኃ-ሕዝብ በፓርላማ ውስጥ ባለ አንድ ፓርቲ ሙሉ ድምፅ እና አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል አማራጭ ሐሳብ ብቻ ሊወከል ፈፅሞ አይችልም፤ ስለዚህ ሕዝቦች ሐሳባቸውን በነጻ የሚገልፁበት ሌሎች አማራጮች ያስፈልጓቸዋል፡፡ እነዚህ አማራጮች ጋዜጣና መጽሔቶችን፣ ሬዲዮና ቴሌቪዥኖችን እንዲሁም አዲሱ ብዙኃን መገናኛ (new media) በመባል የሚታወቀውን በበይነመረብ ላይ ባሉ ድረአምባዎች፣ ጦማሮች እና ማኅበራዊ አውታሮች ላይ ዜጎች የሚያሰፍሯቸውን አስተያየቶች እና ሐሳቦች ያካትታል፡፡

በአሁኑ ወቅት በርካታ በማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያወሩ መጽሔቶች እና ጥቂት የማይባሉ የስፖርት ጋዜጦች ለሕዝብ የሚደርሱ ቢሆንም፣ ማዕከላዊ ትኩረታቸውን ፖለቲካ አድርገው የሚጽፉ ሳምንታዊ ጋዜጦች ቁጥር ግን እየተመናመነ መጥቶ ከ10 በታች ሆኗል፤ ከነርሱም ውስጥ ገሚሱ ከተመሰረቱ 5 ዓመት የማይሞላቸው ሲሆን እንደሌሎቹ ከዚህ በፊት በተለያዩ ምክንያቶች ከስመው እንደቀሩት እልፍ ጋዜጦች መጥፋታቸው አይቀርም የሚል ስጋት አለኝ፡፡ ይህ እንግዲህ የፕሬስ ነጻነት በአገራችን ከተጀመረበት ጊዜ አንጻር ሲታይ በየቀኑ ሁለት፣ ሦስት ጋዜጦች ከሚወጡበት እና የተለያዩ ሐሳቦች ከሚንሸራሸሩበት፣ በቀን ምንም ነጻ ጋዜጣ ላይወጣ ወደሚችልበት (ሰኞ እና ኀሙስን መጥቀስ ይቻላል) ጊዜ ዝቅ ብለናል ማለት ነው፡፡

Wednesday, February 13, 2013

#Valentine’s Day, #Ethiopia: ኢትዮጵያውያን ፍቅር ያውቃሉ?




‹‹ፍቅር ማወቅ እና አለማወቅ›› የሚባል ነገር አለ? ‹‹ፍቅር ማወቅ›› የሚባል ነገር ካለስ - ኢትዮጵያውያን ፍቅር ያውቃሉ? - የዛሬ የፍቅር (የቫለንታይን) ቀን ጽሑፋችን በዚህ ዙሪያ ያጠነጥናል፡፡

መቃጠር (Dating)

“Dating” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል በአገርኛ አማርኛ እኩያ አንድ ቃል ፍቺ ይገኝለት ከተባለ - መቃጠር - የሚለው ተቀራራቢ ይሆናል፡፡ ሆኖም ‹‹አቃጣሪ›› የሚለው የቆየ ቃል የሚሰጠው አሉታዊ ትርጉም ነው፤ ሁለት ሰዎች መሐል ነገር የሚያመላልስ ማለት ሲሆን በፍቅርም ቢሆን አቃጣሪ የሚለው (በተለይም ከጥንታዊ አመጣጡ አንጻር) ቤተሰቦቻቸው ለመገናኘት ዕድሉን የነፈጓቸውን ተፋቃሪዎች በመሐል እየተመላለሰ የፍቅር መልዕክታቸውን የሚያደርስ የሚል ትርጉም ይኖረዋል፡፡ ትርጉሙን ቦርቀቅ ስናደርገው ደግሞ ሁለት ሰዎች እንዲፋቀሩ ለማድረግ በመሐላቸው የድለላ ሥራ የሚሠራ - የሚያቃጥር (dating agent) - እስከሚል ትርጉም ሊደርስ ይችላል፡፡

የፈረንጅኛውን ትርጉም ስንወስደው ደግሞ የተለየ እና አዎንታዊ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ዊኪፔዲያ ለምሳሌ ለDating  የሚሰጠው ትርጉም እንዲህ ይተረጎማል ‹‹Dating is a form of courtship consisting of social activities done by two people with the aim of each assessing the other's suitability as a partner in an intimate relationship or as a spouse. While the term has several meanings, it usually refers to the act of meeting and engaging in some mutually agreed upon social activity in public, together, as a couple.…››

ኢትዮጵያ ውስጥ አንዳንድ ዘመነኛ ከተሜዎች ካልሆኑ በስተቀር፣ መግጠም አለመግጠማችንን እናጥና ብለው ተከታታይ ቀጠሮዎች አመቻችተው፣ አንደኛ፣ ሁለተኛ፣ ሦስተኛ ቀጠሮ በ‹መቃጠር› የሚጠናኑበት እና የሚወያዩበት መንገድ አለ ለማለት ይከብዳል፡፡ አጋጣሚዎች ፈቅደው ከንፈር ለከንፈር ሲገናኙ በሚጀመር የከንፈር ወዳጅነት ድንገት ወደ‹‹ግንኙነት›› ወይም ዕውቅና ያልተሰጠው ፍቅር (affair) ይገባሉ፡፡

ይህንን የመቃጠር ልምድ ማዳበር የግንኙነት ወቅት ለሚኖሩ ክፍተቶችን ለመቀነስ ይረዳል የሚሉ ልምዱ መዳበሩን የሚያበረታቱ ሲኖሩ በሌላ በኩል ደሞ ከባሕላችን ውጪ የሆነና በእኛ ማኅበረሰባዊ ባህሪ ሊለመድምና ውጤታማ ሊሆን አይችልም በሚል ያጣጥሉታል፡፡

ፍቅረኝነት፣ ፍቅር አገላለገጽ እና “Romance”

ልክ እንደ‹dating› ሁሉ ‹romance› ለሚለው ቃልም ሁነኛ የአገርኛ አማርኛ ትርጉም ማግኘት አይቻልም፡፡ ‹romance› ማለት ፍቅርን መግለጫ መንገድ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ጥንዶች ፍቅረኞቻቸውን ለማስደሰት ቢፈልጉም እንኳን ፍቅረኛቸውን ለማስደሰት አቅደው የሚያደርጉበት ልምድ/ባሕል የለም ብሎ መከራከር ይቻላል፡፡ እንዲያውም ብዙዎች የፍቅር አጋራቸውን ‹‹ፍቅረኛዬ›› ነች ብሎ ማለት እያሳፈራቸው፤ በእንግሊዝኛ ‹‹ቦይፍሬንዴ/ገርልፍሬንዴ›› ማለት እየቀናቸው ነው፡፡ ያውም ይህ በከተማ ውስጥ ነው፡፡ በገጠሩ ክፍል በምስጢር ከሚጠበቅ የከንፈር ወዳጅነት ተሻግረው ለትዳር ከበቁ በኋላ ፍቅር የሚገለጸው በቁፍጥንና ነው፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያውያን ብሔሮች እና ባሕሎች ብዙም በማይራራቅ ሁኔታ ባሎች ሚስቶቻቸውን በመቆጣጠር እና በመቆጣት የበላይነታቸውን ከማሳየት በላይ ሌላ ፍቅር የሚገልጹበት መንገድ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ግን ፍቅር የላቸውም ተብሎ ሊተረጎም አይገባም፤ ፍቅር አላቸው ነገር ግን ፍቅራቸውን የመግለጫ መንገድ/ባሕል/ልምድ ግን የላቸውም፡፡ በተደጋጋሚ ሲገለጽ እንደሚስተዋለው ዱላ የፍቅርና ቅናት መገለጫ እየተባለ ቢነሳ አሁን አሁን ግን ጉዳዩ ወንጀል በመሆኑም ጭምር በጊዜ ሂደት ቢያንስ እንደፍቅር መገለጫነት መቆጠሩ ቀርቶአል፡፡

ማቆላመጥ

አንዱ የኢትዮጵያውያን ፍቅርን የመግለጽ ችግርን የሚያንፀባርቀው ፍቅረኞችን ለማቆላመጥ የምንጠቀምበት ቃላት ማጠር ነው፡፡ ፈረንጆቹ ‹‹honey, sweetie, baby…›› እያሉ የፍቅረኛቸው ስም እስኪረሳቸው ሲያቆለማምጡ የኛዎቹ ግን የፍቅረኛቸውን ስም እንኳ በቁልምጫ መጥራት የሚከብዳቸው ጊዜ ይስተዋላል፡፡ ስንቶች ፍቅረኞቻቸውን ‹‹ማሬ፣ ጣፋጯ፣ ፍቅሬ…›› ብለው በአደባባይ ይጠራሉ? ከጓደኞቻቸው ጋርስ በግልጽ ያስተዋውቃሉ? ብዙ ጊዜ ከወጣቶቹ አንደበት የማትጠፋው ‹‹የኔ ቆንጆ›› የምትል ቃል ራሷ፣ የወል ስም እየሆነች አጠቃቀሟ የምር ይሁን የልምድ ለመለየት ያስቸግራል፡፡

Tuesday, February 12, 2013

ሞትን በሕይወት፣ ጥላቻን በፍቅር የረታ ይቅርታ!



በፍቅር ለይኩን

በደቡብ አፍሪካ ኬፕታውን ከተማ የሚገኙ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች፣ ጓደኞቿና የነፃነት ትግሉ አጋሮቿም፡- ‹‹እናዝናለን ኤሚፍቅርሽ፣ ርኅራኄሽ፣ ለሰው ልጆች ነፃነትና መብት መከበር ያለሽ ጽኑ አቋም በልባችን ለዘላለም ይኖራል፡፡ ትግላችን እንዳቺ ያሉ የእውነት፣ የፍትሕ ጠበቃዎችንና ሐቀኞችን በአጥፍ ጨምሮ ይቀጥላል፡፡ ኤሚ እንወድሻለን፣ ሁሌም እናስታውስሻለን! አንቺ የዘረኞችን የመለያየት ግንብ የናድሽ ጀግናችን ነሽ፣ አንቺ በልባችን ውስጥ ለዘላለም ሕያው ነሽሞት በአንቺ ላይ ስልጣን የለውም፣ ሞትን በሕይወት፣ ጥላቻን በፍቅር ያሸነፈሽ የሕዝባችን ታላቅ ሰማዕት ነሽና …!›› በማለት ወደ ትውልድ አገሯ አሜሪካ በእንባና በመሪር ሐዘን ሸኟት፡፡
                                                   
ውቧ፣ ማራኪዋና ከዓለማችን አስር ምርጥ ከተሞች ተርታ የተመዘገበችው የደቡብ አፍሪካዋ የኬፕታውን ከተማ የደቡብ አፍሪካ የታሪክ፣ የቅርስ፣ የባህልና የፖለቲካ ማዕከል ናት፡፡ የድኅረ ምረቃ ትምህርቴን የተከታተልኩባት ኬፕታውን ለአምስት መቶ ዓመታት ያህል አፍሪካውያን ያለፉበትን ውስብስብ የታሪክ ጉዞ የሚያስቃኙ፣ የጥቁር ሕዝቦችን የአይበገሬነትና የነፃነት ተጋድሎ የሚዘክሩ በርካታ ቅርስና ሕያው አሻራ ያላት ታሪካዊ ከተማ ናት፡፡

ኬፕታውን ታላቁ አፍሪካዊ የነፃነት አርበኛ ኔልሰን ማንዴላና የትግል አጋሮቻቸው ለ27 ዓመታት የተጋዙባትን ቀዝቃዛውን የአትላንቲክ ውቅያኖስንና የከተማይቱን ግርማና ውበት የሆነውን የቴብል ማውንቴንን ተንተርሶ የተገነባው የሮቢን ደሴየት ግዞት ቤት/ወኅኒ ቤት የሚገኝባትም ናት፡፡

ይህን ለዘመናት በርካታ አፍሪካውያንና ጥቁር ሕዝቦች ለሰው ልጆች ነፃነትና ሰብአዊ መብት ሲሉ የተጋዙበትን የሮቢን ደሴየት ግዞት ቤት/ወኅኒ ቤት በየቀኑ በሺህዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎች፣ የታሪክ ተመራማሪዎችና አጥኚዎች፣ ፖለቲከኞች፣ መሪዎች፣ ታላላቅ የሆኑ የዓለማችን የፊልም እንዱስትሪዎችና ባለሙያዎች እንዲሁም ዝነኞችና ባለ ጠጋዎች ይጎበኙታል፡፡ እናም የደቡብ አፍሪካዋ ‹‹እናት ከተማ›› ኬፕታውን የቱሪስቶችና ውብ የመዝናኛ ከተማም ጭምር ናት፡፡

በዩኒቨርስቲ ቆይታዬ በትምህርት ክፍላችንና የድኅረ ምረቃ ፕሮግራሙን ነፃ የትምህርት ዕድልና አጠቃላይ ወጪያችንን የሸፈነልን የሮቢን ደሴየት ሙዚየም፣ በኬፕታውን የሚገኙትን ቤተ መዘክሮችን፣ የደቡብ አፍሪካውያንን የነፃነት ተጋድሎ የሚያንጸባርቁ ታሪካዊ ቦታዎችንና ቅርሶችን መጎብኘት እንድንችል ዕድልን አመቻችቶልን ነበር፡፡ በዚህ ዕድልም ከጎበኘኋቸውና በማስታወሻ ደብተሬ ከመዘገብኳቸው አስደናቂ ስፍራዎች መካከል አንዱ ለዛሬ ጽሑፌ መነሻ ሆኖኛል፡፡

እኔና የክፍል ጓደኞቼ ጉብኝታችን ፕሮግራሞች ውስጥ ካየናቸው የአፓርታይድ አገዛዝን ጭካኔና ክፋት ከሚዘክሩ ታሪካዊ ቦታዎች በኬፕታውን ከተማ የሚገኘው የጉጉሌቱ ታውን ሺፕ አንዱ ነው፡፡ ይህ ታውን ሺፕ/መንደር በአብዛኛው ጥቁሮች የሚኖሩበት ነው፡፡