Saturday, July 7, 2012

የኪራይ ሰብሳቢ ማዕበል

በዘላለም ክብረት
“Rent-seeking may, indeed, impose costs to the economy as high, if not higher, than those arising from corruption.”
  Anthony Ogus , Corruption and Regulatory Structures.

ገንዘብን መግዛት (Rent seeking)

በስነ ምጣኔ ሳይንስ ከእያንዳንዱ ኢኮኖሚ ጀርባ ብዙ ጋሬጣዎች(Economic Inefficiencies) ሊኖሩ ይችላሉ ለምሳሌ እንደ ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት፣ የገንዘብ እና የፊስካል ፖሊሲ ክፍተት፣ ሙስና ፣ ገንዘብን መግዛት (Rent seeking) ወ.ዘ.ተ ናቸው፡ ከነዚህ የኢኮኖሚ ማነቆዎች ውስጥ ገንዘብን መግዛት (Rent seeking) የተባለውን ስንመለከት፡፡በአጠቃለይ ኢኮኖሚስቶች ‹‹እሴት አልባ ትርፍ ወይም አሁን ያለው ገንዘብ በራሱ ያለምንም ዕሴት ማጎልበት ተጨማሪ ገንዘብ እንዲገዛ ለዛ መበርታት›› ብለው ይተረጉሙታል፡፡

John Mbaku የተባሉ ኢኮኖሚስት ‘Corruption and Rent-seeking’ ባሉት ፅሁፋቸው ገንዘብን መግዛትን ‹‹የመንግስት ፖሊሲዎችን ውጤት ለማስቀየር የሚደረግ እንቅስቃሴ›› ብለው ይተረጉሙታል ፡፡ የገንዘብን መግዣ ድርጊቶች ስንመለከት የተያዩ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

Anne Kruger የተባሉ የሚኒሶታ ዩንቨርስቲ ኢኮኖሚስትThe Political Economy of Rent-Seeking Economy’ ባሉት ፅሁፋቸው ‹‹ገንዘብን ለመግዛት የሚደረገው ውድድር አንዳንዴ ንፁህ እና ህጋዊ በሆነ መልኩ አንዳንዴ ደግሞ እንደ ሙስና፣ ጥቁር ገበያ እና ህገወጥ የዕቃ ማስተላለፍ ያሉትን ህገወጥ መንገዶች በመጠቀም ሊከናወን ይችላል›› ይላሉ፡፡ ይሄም ገንዘብን መግዛት ሁሌም ህገወጥ ተግባር ብቻ አይደለም ወደሚለው መደምደሚያ ያደርሰናል ማለት ነው፡፡


John Mbaku ከላይ በተጠቀሰው ፅሁፋቸው በታዳጊ ሀገራት የገንዘብን መግዛት ተግባር በስፋት የሚታይ እንደሆነ ይሄም በከተሞች ጎላ ብሎ እንደሚታይ እና ከገንዘብን መግዥ ተግባራት ማነኞቹ ቢሮክራሲያዊ ሙስና እና የፖለቲካ አመፅ ማስነሳት መሆኑን ይጠቅሳሉ፡፡ አያይዘውም ‹‹በመንግስት የተያዙ ሞኖፖሊዮች ለገንዘብን መግዣ ተግባራት ዋነኛዎቹ መፈልፈያዎች ናቸው›› ይላሉ፡፡ ‹‹ምክንያቱም እነዚህ ኖፖሊዩች ተወዳዳሪ ስለሌላቸው ገንዘብን እንደፈለጉ ያደኑታል ያለምንም ማህበራዊ አበርክቶ ደንበኞችም ያለምንም አማራጭ የቀረበላቸውን አገልግሎት ይጠቀማሉ፡፡››

ኪራይ ሰብሳቢነት ስንል

ኢትዩጵያ ውስጥ የገንዘብን መግዣ (Rent Seeking) ፅንሰ ሃሳብ ከሶሻሊዝም ጋር አብሮ እንደጎለበተ ለማየት ይቻላል እንደ ካፒታሊዝም ውድቀት ተደርጎ በመወሰድ፡፡ በዋነኛነት ግን የህብረተሰቡ ተወስኦ(Public Discourse) አካል እየሆነ የመጣው ከ1997 ዓ.ም ሀገር አቀፍ ምርጫ በኋላ ነው ማለት ይቻላል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ‘AFRICAN DEVELOPMENT: DEAD ENDS AND NEW BEGINNINGS’ ባሉት እና ከ600 ገፅ በላይ እንዳለው የተነገረውን የዶክትሬት ዲግሪ ማሟያቸውን ከሆነው ፅሁፍ ውስጥ የመጀመሪያ ደረጃ ረቂቅ (Preliminary Draft) ላይ በ50 ገፅ ቁራጭ ታሪኮች (Excerpts) ፅሁፍ እ.አ.አ በ2006 ዓ.ም አቅርበዋል፣ ለውይይት አላማ በሚል፡፡ የዚህ ፅሁፍ ዋነኛ ማጠንጠኛም ይሄው የገንዘብን መግዛት (Rent Seeking) ፅንሰ ሀሳብ ነው፡፡ ለዛም ይመስላል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ 50 ገፅ አካባቢ ፅሁፍ ውስጥ ወደ መቶ ለሚጠጋ ጊዜ Rent Seeking የሚለውን ቃል ይደጋግሙታል፡፡ አንድ ምዕራፍም በአፍሪካ ያለውን የገንዘብን መግዛት (Rent Seeking) ፖለቲካል ኢኮኖሚን ለመተንተን አውለዋል፡፡

እንደ መደምደሚያም “Only when there is a state that has the characteristics of a developmental state can one meaningfully discuss the elimination of rent-seeking behavior. In its absence rent-seeking will be rampant no matter what the size of the state might be.” በማለት የገንዘብን መግዛት ክፉ ጠንቅን የሚዋጋው ልማታዊ መንግስት (Developmental State ) እንጅ ከዳር ቆሞ የሚመለከት መንግስት (Night watch man State) አይደለም በማለት ሀሳባቸውን ያሳርፋሉ፡፡

እንግዲህ በኢትዮጵያ የገንዘብን መግዛት ፅንሰ ሀሳብ ‘ኪራይ ሰብሳቢነት’ በሚል ስም ዋነኛ የውይይት አርዕስት የሆነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከላይ የጠቀስነውን ፅሁፍ ይፋ ካደረጉ በኋላ ነው፡፡ የኢህአዴግ ዋነኛ ልሳኖችም ጉዳዩን ለህብረተሰቡ በሰፊው ማቀበል የጀመሩት ከዚህ ጊዜ በኋላ ነው በኋላ ላይ ከፓርቲው ልሳኖች በተጨማሪ የመንግስት የሚዲያ ተቋማትም ጉዳዩ የሀገሪቱ ታላቅ ስጋት እንደሆነ አድርገው እያቀረቡት ይገኛሉ፡፡

‹‹ደላሎችን በሙሉ ኪራይ ሰብሳቢ ናቸው ማለት ተገቢ አይደለም››

ይህ አንድ የደላላ ማህበር ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ የፃፈው ደብዳቤ ርዕስ ነው፡፡ አሁን ባለው አካሄድ መንግስት በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ ዜጎችን በ2 ጎራ ከፍሏል ማለት ይቻላል፡፡ የልማታዊነት ጎራ እና የኪራይ ሰብሳቢነት ጎራ፡፡ ኪራይ ሰብሳቢው ማነው? ካላችሁ እስከ አሁን ድረስ በፓርቲው ሰነዶች ውስጥ ግልፅ ትርጉም አልተሰጠውም ይልቅስ ድርጊቶችን ብቻ በመጥቀስ ይሄ ኪራይ ሰብሳቢነት ነው ይሄ ልማታዊነት ነው በማለት እየተገለፀ ነው፡፡

ጨዋታ ነውና ጉዳዩን እንደሚከተለው እንየው እስኪ ፡

* ኪራይ ሰብሳቢነት ምንድን ነው?

- እስከ አሁን የተገለፀ ነገር የለም፡፡

* የኪራይ ሰብሳቢነት ምንጮች ምንድን ናቸው?

- ‹‹ኪራይ ሰብሳቢው በዋነኛነት የመሸገባቸው፣ መሬት፣ ግብር፣ ንግድ፣ የመንግስት ግዥ አሰራሮች ናቸው›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 8 ገፅ 45-46

* ኪራይ ሰብሳቢነት በመንግስት መስሪያቤቶች ውስጥ እንዴት ይገለፃል?

- ‹‹የመንግስት መዋቅሩ የኪራይ ሰብሳቢነት ፍርፋሪ በመለቃቀም የተጨማለቀ ወይም ከዛሬ ነገ ፍርፋሪ ይጣልልኝ ይሆናል ብሎ የሚጠብቅ ሰው ያልተለየው መዋቅር ነው፡፡ የኪራይ ሰብሳቢነት የውስጥ አርበኛ ነው፡፡›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 8 ገፅ 28-29 እያለ የመንግስት ሰራተኛውን ይከሳል እንዲያም ሲል 'የመንግስት ሌቦች' ይለዋል፡፡

* ኪራይ ሰብሳቢነት በጥቅሉ በሀገሪቱ እንዴት ይገለፃል?

- ‹‹ከአስር አመታት በፊት የሀገራችን ኢኮኖሚ ሙሉ በሙሉ ለኪራይ ሰብሳቢነት የተመቸ እና ኪራይ ሰብሳቢው የሚቆጣጠረው ነበር፡፡ኪራይ ሰብሳቢነትን የመታገል እና የማዳከም ስራችን በመሰረቱ በትክክለኛ አቅጣጫ እየተጓዘ ነው ፡፡ አደጋውን ለይተናል ምንጩን እና የትግል አግባቡን አስቀምጠናል፡፡ ተግባራዊ ትንቅንቅ ጀምረናል፡፡›› እንዲሁም ‹‹ኪራይ ሰብሳቢው መግቢያ መውጫውን ከማወቁ እና የቁማርተኛ አይነት ድፍረት ተጠናወተው በመሆኑ ከእያንዳንዱ እንቅስቃሴው ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለማግኝት ከሚገባው በላይ ተግቶ እየሰራ ይገኛል፡፡›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 8 ገፅ 45

* ኪራይ ሰብሳቢነትን በዋናነት መታገል ያለበት ማነው? ብላችሁ ስትጠይቁ ደግሞ፡

- ‹‹የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ተግባር በመታገል ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የዜግነት ግዴታ ያለበት ቢሆንም መምህራን ካለባቸው ብቁ ዜጋ የመቅረፅ ኃላፊነት አኳያ ያለባቸው ኃላፊነት ድርብ ነው፡፡›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 9 ገፅ 54 ብሎ መምህሩን ሀላፊነት ይሰጠዋል፡፡

* የኪራይ ሰብሳቢነት እና የዕምነት ግንኙነት እንዴት ነው ካላችሁ?

- ‹‹አክራሪነትን ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር አስተሳስረን እንፋለመዋለን›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 9 ገፅ 38 እንዲሁም ‹‹አክራሪነትን ከኪራይ ሰብሳቢነት ነጥለን መታገል አንችልም›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 9 ገፅ 40 በማለት የኪራይ ሰብሳቢነትን አድማስ ከአክራረነት ጋር አያይዞ ያየዋል፡፡

* Where is the Rendezvous of this ‘ኪራይ ሰብሳቢነት’? ካላችሁ መልሱ :

- ‹‹የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከቶች በከተሞች ሰፋ ያለ አድማስ አላቸው፡፡›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 9 ገፅ 31

* ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዴት ይታያሉ?

- ‹‹በሀገራችን የሚገኝው የተቃውሞ ቡድን ባነገበው አላማና በኪራይ ሰብሳቢነቱ አንድ ነው፡፡›› አዲስ ራዕይ ጋቢት ሚያዚያ 2002 ገፅ 4

* ለመሆኑ ኪራይ ሰብሳቢነት በህግ ያስቀጣል?

- ‹‹ዋናዎቹን ኪራይ ሰብሳቢዎች ወደመቅጣት የምንገባው ከመጥፎ ተግባር አልላቀቅ ሲሉና ማረሚያ ሌላ አማራጭ ሲጠፋ ነው፡፡›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 2 ቅፅ 3 ቁጥር 8 ገፅ 33

* በአጠቃለይ ከኢትዮጵያዊያን ምን ይጠበቃል?

- ‹‹የልማት አብዮቱን ለማጎልበት ኪራይ ሰብሳቢነትን ለቀቅ ልማታዊነትን ጠበቅ›› አዲስ ራዕይ ቁጥር 6 ቅፅ 3 ቁጥር 8 ገፅ 36 እያለ ፓርቲው ምላሽ ይሰጣል ጉዳዩንም ከመሬት ወራሪዎች እስከ ፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች እንዲሁም መምህሩን እና የሀይማኖት መሪዎችን እየነካካ መጨረሻ የሌለው እስኪመስል ድረስ ይጓዛል፡፡ ይሄን ስንመለከትም ኪራይ ሰብሳቢነትን እንረዳው ዘንድ ይከብድብናል፡፡ ምን ማለት ይሆን? ያስብለናል::

ለማንኛውም፡

‹‹ጉልበተኛ ይሰይማል፡፡ መሰየም የጉልበተኛ አንዱ እና ትልቁ አቅም ነው፡፡ አንተ ሽብረተኛ ነህ ምክንያቱም ፂምህ ከደረትህ ደርሷልና፣ አንች ያለፈውን ስርዓት ናፋቂ ነሽ ምክንያቱም አባትሽ ለንጉሱ ስርዓት አፋሽ አገንባሽ ነበርና፣ አንተ መንግስትን በሀይል ለመገልበጥ ከሚሰሩ ህሎች አንዱ እና ዋነኛው ነህ ምክንያቱም ሀምሌ 27 የተባለ ፓርቲ ልሳን እቤትህ ተገኝቷልና ወ.ዘ.ተ እያለ ስያሜው ይቀጥላል፡፡ ምክንያቱም ጉልበተኛ ሲሰይም ማንም ተው አይለውምና፡፡››

No comments:

Post a Comment